መዝሙር 87 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)የቆሬ ልጆች የምስጋና መዝሙር። ለመዘምራን አለቃ በማኸላት ለመዘመር የይዝራኤላዊው የኤማን ትምህርት። 1 የድኅነቴ አምላክ እግዚአብሔር፥ በቀንና በሌሊት በፊትህ ጮኽሁ፤ 2 ጸሎቴ ወደ ፊትህ ትግባ፥ ጆሮህንም ወደ ልመናዬ አዘንብል፤ 3 ነፍሴ መከራን ጠግባለችና፥ ሕይወቴም ለሞት ቀርባለችና። 4 ወደ ጕድጓድ ከሚወርዱ ጋር ተቈጠርሁ፥ ረዳትም እንደሌለው ሰው ሆንሁ። 5 እንደ ተገደሉና በመቃብር ውስጥ እንደ ተጣሉ፥ ለዘለዓለም እንደማታስባቸው በሙታን መካከል የተጣልሁ ሆንሁ፤ እነርሱ ከእጅህ ርቀዋልና። 6 በጨለማና በሞት ጥላ ውስጥ፥ በታችኛው ጕድጓድ አስቀመጡኝ። 7 በእኔ ላይ ቍጣህ ጸና፥ መቅሠፍትህን ሁሉ በእኔ ላይ አመጣህ። 8 የሚያውቁኝን ከእኔ አራቅህ፤ በእነርሱ ዘንድ ርኩስ አደረግኸኝ፤ ያዙኝ፥ መውጫም የለኝም። 9 ዐይኖቼም በችግር ፈዘዙ፤ አቤቱ፥ ሁልጊዜ ወደ አንተ ጮኽሁ፥ እጆቼንም ወደ አንተ ዘረጋሁ። 10 በውኑ ለሙታን ድንቅን ታደርጋለህን? ወይስ ያመሰግኑህ ዘንድ ባለ መድኀኒቶች ያነሡአቸዋልን? 11 በመቃብርስ ውስጥ ያሉት ቸርነትህን፥ እውነትህንስ በሞት ስፍራ ይናገራሉን? 12 ተአምራትህ በጨለማ ይታወቃልን? ቅንነትህስ በምድር ተረሳን? 13 አቤቱ፥ እኔ ግን ወደ አንተ ጮኽሁ፤ በጥዋት ጸሎቴ ወደ አንተ ትድረስ። 14 አቤቱ፥ ጸሎቴን ለምን ትጥላለህ? ፊትህንስ ከእኔ ለምን ትመልሳለህ። 15 እኔ ድሃ ነኝ፥ ከሕፃንነቴ ጀምሮ ደከምሁ። ከፍ ከፍ ካልሁ በኋላ ተዋረድሁ፥ ተናቅሁም። 16 መቅሠፍት በላዬ አለፈ፥ ግርማህም አስደነገጠኝ። 17 ሁልጊዜ እንደ ውኃ ከበቡኝ፥ በአንድነትም ያዙኝ። 18 ወዳጆቼንና ባልንጀሮቼን ዘመዶቼንም ከችግሬ የተነሣ ከእኔ አራቅህ። |