መዝሙር 82 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)የአሳፍ የምስጋና መዝሙር። 1 አቤቱ፥ እንደ አንተ ማን ነው? አቤቱ፥ ዝም አትበል፥ ቸልም አትበል። 2 እነሆ፥ ጠላቶችህ ጮኸዋልና፥ ጠላቶችህም ራሳቸውን አንሥተዋልና። 3 ሕዝብህን በምክር ሸነገሉአቸው፥ በቅዱሳንህም ላይ ተማከሩ። 4 “ኑ ከሕዝብ ለይተን እናጥፋቸው፥ ከእንግዲህም ወዲህ የእስራኤልን ስም አያስቡ” አሉ። 5 በአንድነት ተካክለው ተማክረዋልና፤ በአንተ ላይ ሤራ ቈረጡ፤ ቃል ኪዳንም አደረጉ፤ 6 የኤዶምያስ ወገኖች፥ እስማኤላውያንም፥ ሞዓባውያንም፥ አጋራውያንም፥ 7 ጌባል፥ አሞንም፥ አማሌቅም፥ ፍልስጥኤማውያንም ከጢሮስ ሰዎች ጋር፤ 8 አሦርም ከእነርሱ ጋር ተባበረ፥ ለሎጥ ልጆችም ረዳት ሆኑአቸው። 9 እንደ ምድያምና እንደ ሲሣራ፥ በቂሶንም ወንዝ እንደ ኢያቢስ አድርግባቸው። 10 እንደ ዕንዶር ሰዎች ይጥፉ እንደ ምድር ትቢያ ይሁኑ። 11 አለቆቻቸውን እንደ ሔሬብና እንደ ዜብ፥ ታላላቆቻቸውንም ሁሉ እንደ ዛብሄልና እንደ ስልማና አድርጋቸው። 12 የእግዚአብሔርን መሠዊያ እንወርሳለን የሚሉትን። 13 አምላኬ ሆይ፥ እንደ መንኰራኵር፥ በእሳት ፊትም እንደ አለ ገለባ አድርጋቸው። 14 እሳት ዱርን እንደሚያቃጥል፥ ነበልባልም ተራሮችን እንደሚያነድድ፥ 15 እንዲሁ በቍጣህ አሳድዳቸው፥ በመቅሠፍትህም አስደንግጣቸው። 16 በፊታቸው እፍረትን ሙላ፥ አቤቱ፥ ስምህን ይወቁ። 17 ይፈሩ፥ ለዘለዓለሙም ይታወኩ፤ ይጐስቍሉ፥ ይጥፉም። 18 ስምህም እግዚአብሔር እንደ ሆነ፥ በምድር ሁሉ ላይም አንተ ብቻ ልዑል እንደ ሆንህ ይወቁ። |