መዝሙር 77 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)የአሳፍ ትምህርት። 1 ሕዝቤ ሆይ፥ ሕጌን አድምጡ፥ ጆሮአችሁንም ወደ አፌ ቃል አዘንብሉ። 2 አፌን በምሳሌ እከፍታለሁ፤ ከቀድሞ ጀምሮ ያለውንም ምሳሌ እናገራለሁ። 3 የሰማነውንና ያየነውን፥ አባቶቻችንም የነገሩንን፥ ለሚመጣ ትውልድ ከልጆቻቸው አልሰወሩም። 4 የእግዚአብሔርን ምስጋና ተናገሩ፥ ኀይሉንና ያደረገውንም ተአምራት። 5 ለያዕቆብ ያቆመውን ምስክር፥ ለእስራኤልም የሠራውን ሕግ፥ ለአባቶቻችን ያዘዘውን ለልጆቻቸው ይነግሩ ዘንድ፥ 6 የሚመጣ ትውልድ የሚወለዱም ልጆች ያውቁ ዘንድ፥ ተነሥተውም ለልጆቻቸው ይነግራሉ። 7 ተስፋቸውን በእግዚአብሔር እንዲያደርጉ፥ የእግዚአብሔርንም ሥራ እንዳይረሱ፥ ትእዛዙንም እንዲፈልጉ፤ 8 እንደ አባቶቻቸው እንዳይሆኑ፥ ጠማማና የምታስመርር ትውልድ፥ ልብዋን ያላቀናች ትውልድ፥ መንፈስዋ በእግዚአብሔር ዘንድ ያልታመነች። 9 የኤፍሬም ልጆች ቀስታቸውን ገትረው ይወጉ ነበር። በሰልፍ ቀን ወደ ኋላ ተመለሱ። 10 የእግዚአብሔርን ኪዳን አልጠበቁምና፥ በሕጉም ለመሄድ እንቢ አሉ፤ 11 ረድኤቱንና ያሳያቸውን ተአምራቱን ረሱ፥ 12 በግብጽ ሀገርና በጣኔዎስ በረሃ በአባቶቻቸው ፊት የሠራውን ተአምራት። 13 ባሕርን ከፍሎ አሳለፋቸው፤ ውኆችን እንደ ረዋት ውኃ አቆመ። 14 ቀን በደመና መራቸው፥ ሌሊቱንም ሁሉ በእሳት ብርሃን። 15 ዓለቱን በምድረ በዳ ሰነጠቀ፤ ከብዙ ጥልቅ እንደሚገኝ ያህል አጠጣቸው። 16 ውኃንም እንደ ወንዞች አፈሰሰ። ውኃንም ከዓለት አፈለቀ፥ 17 ነገር ግን እርሱን መበደልን እንደገና ደገሙ፥ ልዑልንም በምድረ በዳ አስመረሩት። 18 ለነፍሳቸው መብልን ይፈልጉ ዘንድ፥ እግዚአብሔርን በልባቸው ፈተኑት። 19 እግዚአብሔርን እንዲህ ብለው አሙት፦ “እግዚአብሔር በምድረ በዳ ማዕድን ያሰናዳ ዘንድ 20 ዓለቱን ይመታ ዘንድ ውኃንም ያፈስ ዘንድ ይችላልን? እንጀራን መስጠትና ለሕዝቡስ ማዕድን መሥራት ይችላልን?” 21 እግዚአብሔርም ይህን ሰምቶ ተቈጣ፤ በያዕቆብም ላይ እሳት ነደደ፥ መቅሠፍትም በእስራኤል ላይ ወጣ፤ 22 በእግዚአብሔር አላመኑምና፥ በማዳኑም አልተማመኑምና። 23 ደመናውንም ከላይ አዘዘ፥ የሰማይንም ደጆች ከፈተ፤ 24 ይበሉም ዘንድ መናን አዘነበላቸው፥ የሰማይንም እንጀራ ሰጣቸው። 25 የመላእክትንም እንጀራ የሰው ልጆች በሉ። የሚበቃቸው ስንቅንም ላከላቸው። 26 ከሰማይ ዐዜባዊ ነፋስን አስነሣ፥ በኀይሉም መስዓዊ ነፋስን አመጣ፤ 27 ሥጋን እንደ አፈር፥ የሚበርሩትንም ወፎች እንደ ባሕር አሸዋ አዘነበላቸው፤ 28 በሰፈራቸው መካከል፥ በድንኳናቸውም ዙሪያ ወደቀ። 29 በሉ፥ እጅግም ጠገቡ፤ ለምኞታቸውም ሰጣቸው። 30 ከወደዱትም አላሳጣቸውም፤ መብላቸውም ገና በአፋቸው ሳለ፥ 31 የእግዚአብሔር መቅሠፍት በላያቸው መጣ፥ ከእነርሱም ብዙዎቹን ገደለ፤ የእስራኤልንም ምርጦች አሰናከለ። 32 ከዚህም ሁሉ ጋር እንደ ገና እርሱን በደሉ፥ ተአምራቱንም አላመኑም፤ 33 ቀኖቻቸውም በከንቱ አለቁ፥ ዓመቶቻቸውም በችኮላ አለፉ። 34 በገደላቸውም ጊዜ ወዲያው ፈለጉት፤ ተመለሱ፥ ወደ እግዚአብሔርም ገሠገሡ፤ 35 ረዳታቸውም እግዚአብሔር፥ መድኀኒታቸውም ልዑል እግዚአብሔር እንደ ሆነ ዐሰቡ። 36 በአፋቸው ብቻ ወደዱት፤ በአንደበታቸውም ዋሹበት፤ 37 ልባቸውም ከእርሱ ጋር አልቀናም፥ በቃል ኪዳኑም አልተማመኑትም። 38 እርሱ ግን መሐሪ ነው፥ ኀጢአታቸውንም ሁሉ ይቅር አላቸው፥ አላጠፋቸውምም፤ ቍጣውንም መመለስ አበዛ፥ መዓቱንም ሁሉ አላቃጠለም። 39 ሥጋም እንደ ሆኑ ዐሰበ። መንፈስ ከወጣ በኋላ አይመለስም 40 በምድረ በዳ ምን ያህል አስቈጡት፥ በበረሃም አሳዘኑት። 41 ተመለሱ፥ እግዚአብሔርንም ፈተኑት፥ የእስራኤልንም ቅዱስ አሳዘኑት። 42 እነርሱም እጁን አላሰቡም፥ ከጠላቶቻቸው እጅ ያዳነበትን፥ 43 በግብፅ ያደረገውን ተአምራቱን፥ በጣኔዎስም በረሃ ያደረገውን ድንቁን። 44 ወንዞቻቸውንም ወደ ደም ለወጠ፥ ምንጮቻቸውንም ደግሞ እንዳይጠጡ። 45 ዝንቦችንም በላያቸው ሰደደባቸው፥ በሉአቸውም፤ ጓጕንቸሮችን ሰደደ፥ አረከሳቸውም። 46 ፍሬያቸውን ለኩብኩባ፥ ሥራቸውንም ለአንበጣ ሰጠ። 47 ወይናቸውንም በበረዶ፥ በለሳቸውንም በውርጭ አጠፋ። 48 እንስሶቻቸውን ለበረዶ፥ ሀብታቸውንም ለእሳት ሰጠ። 49 የመዓቱን መቅሠፍት በላያቸው ሰደደ፤ መቅሠፍትን፥ መዓትንም መከራንም በክፉዎች መላእክት ሰደደ። 50 ለቍጣው መንገድን ጠረገ፤ ነፍሳቸውንም ከሞት አላዳናትም፥ እንስሶቻቸውንም በሞት ውስጥ ዘጋ፤ 51 በኵሮቻቸውንም ሁሉ በግብፅ ምድር፥ የድካማቸውንም መጀመሪያ በቤቶቻቸው ውስጥ ገደለ። 52 ሕዝቡን ግን እንደ በጎች አሰማራቸው፥ እንደ መንጋም ወደ ምድረ በዳ አወጣቸው። 53 በተስፋም መራቸው አልፈሩምም፥ ጠላቶቻቸውንም ባሕር ደፈናቸው። 54 ወደ መቅደሱም ተራራ ወሰዳቸው፥ ቀኙ ወደ ፈጠረችው ተራራ፤ 55 ከፊታቸውም አሕዛብን አባረረ፥ ርስቱንም በገመድ አካፈላቸው፥ የእስራኤልንም ወገኖች በቤታቸው አኖረ። 56 ነገር ግን ልዑል እግዚአብሔርን ፈተኑት፥ አሳዘኑትም፥ ምስክሩንም አልጠበቁም፤ 57 ተመለሱም፥ እንደ አባቶቻቸውም ከዱ፤ እንደ ጠማማ ቀስትም ሆኑ፤ 58 በኮረብቶቻቸውም አስቈጡት፥ በተቀረጹ ምስሎቻቸውም አስቀኑት። 59 እግዚአብሔርም ይህን ሰምቶ ተቈጣ። እስራኤልንም እጅግ ናቃቸው፤ 60 የሴሎምንም ድንኳን ተዋት፥ በሰዎች መካከል ያደረባትን ድንኳኑን። 61 ኀይላቸውን ለምርኮ፥ ጌጣቸውንም በጠላት እጅ ሰጠ። 62 ሕዝቡንም በጦር ውስጥ ዘጋቸው፥ ርስቱንም ቸል አላቸው። 63 ጐልማሶቻቸውን እሳት በላቻቸው፥ ቈነጃጅቶቻቸውም አላለቀሱም። 64 ካህኖቻቸውም በሰይፍ ወደቁ፥ ባልቴቶቻቸውም አላለቀሱላቸውም። 65 እግዚአብሔርም ከእንቅልፍ እንደሚነቃ ተነሣ፥ የወይን ስካር እንደ ተወው እንደ ኀያልም ሰው፤ 66 ጠላቶቹንም በኋላው ገደለ፤ የዘለዓለምንም ኀሣር ሰጣቸው። 67 የዮሴፍንም ድንኳን ተዋት፥ የኤፍሬምንም ወገን አልመረጠውም፤ 68 የይሁዳን ወገን ግን መረጠ፥ የወደደውን የጽዮንን ተራራ። 69 መቅደሱን እንደ አርአያም ሠራ፥ ለዘለዓለምም በምድር ውስጥ መሠረታት። 70 ባሪያው ዳዊትንም መረጠው፥ ከበጎቹም መንጋ ውስጥ ወሰደው፤ 71 ከሚያጠቡ በጎችም በኋላ፥ ባሪያውን ያዕቆብን ርስቱን እስራኤልንም ይጠብቅ ዘንድ ወሰደው። 72 በልቡ ቅንነት ጠበቃቸው፥ በእጁም ጥበብ መራቸው። |