መዝሙር 69 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)ለመዘምራን አለቃለመታሰቢያ የዳዊት መዝሙር። 1 አቤቱ፥ እኔን ለማዳን ተመልከት፤ አቤቱ፥ እኔን ለመርዳት ፍጠን። 2 ነፍሴን የሚሹአት ይፈሩ፥ ይጐስቍሉም፥ ክፉንም የሚመክሩብኝ ወደኋላቸው ይመለሱ፥ ይፈሩም። 3 እሰይ! እሰይ! የሚሉኝ አፍረው ወዲያው ወደ ኋላቸው ይመለሱ። 4 አቤቱ፥ የሚሹህ ሁሉ በአንተ ሐሤት ያድርጉ፥ ደስም ይበላቸው፤ ሁልጊዜ ማዳንህን የሚወድዱ፥ “ዘወትር እግዚአብሔር ታላቅ ነው” ይበሉ። 5 እኔ ድሃና ምስኪን ነኝ፤ እግዚአብሔርም ይረዳኛል፤ ረዳቴ መጠጊያዬም አንተ ነህ፥ አቤቱ አምላኬ አትዘግይ። |