መዝሙር 64 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)ለመዘምራን አለቃ የዳዊት የምስጋና መዝሙር። 1 አቤቱ፥ በጽዮን ለአንተ ምስጋና ይገባል፥ ለአንተም በኢየሩሳሌም ጸሎት ይቀርባል። 2 ወደ አንተ የሚመጣ የሰውን ሁሉ ጸሎት ስማ 3 የዐመፀኞች ነገር በረታብን፤ ኀጢአታችንንስ አንተ ይቅር ትላለህ። 4 አንተ የመረጥኸው በአደባባዮችህም ለማሳደር የተቀበልኸው ብፁዕ ነው፤ አቤቱ፥ ከቤትህ በረከት ጠገብን። 5 ቤተ መቅደስህ ቅዱስ ነው በጽድቅም ድንቅ ነው። በምድር ዳርቻ ሁሉና በሩቅ ባሕር ውስጥ ላሉ ተስፋቸው የሆንህ፥ አምላካችንና መድኃኒታችን ሆይ ስማን። 6 በኀይልህ ተራሮችን አጸናሃቸው፥ እነርሱም በኀይል ታጥቀዋል። 7 የባሕሩን ዓሣ አንበሪ የሚያውከው እርሱ ነው የሞገድዋንም ድምፅ የሚቃወመው ማን ነው? 8 ከተአምራትህ የተነሣ አሕዛብ ይደንግጣሉ፥ በምድር ዳርቻም የሚኖሩ ይፈራሉ፤ በጥዋት ይወጣሉ፥ ማታም ይደሰታሉ። 9 ምድርን ጐበኘሃት አረካሃትም፥ ብልጽግናዋንም እጅግ አበዛህ፤ የእግዚአብሔር ወንዝ ውኆችን የተመላ ነው፤ ምግባቸውን አዘጋጀህ፥ እንዲሁ ታሰናዳለህና። 10 ትልምዋን አርካው፥ መከሯንም አብጀው፤ በነጠብጣብህም ደስ ብሏት ትበቅላለች 11 የምሕረትህን ዓመት አክሊል ትባርካለህ ምድረ በዳዎችም ጠልን ይጠግባሉ። 12 የምድረ በዳ ተራሮች ይረካሉ፥ ኮረብቶችም በደስታ ይታጠቃሉ። 13 የበጎች አውራዎችም ስብን ይለብሳሉ፥ ሸለቆዎችም ስንዴን ይመላሉ፤ እየጮሁ ያመሰግናሉ። |