መዝሙር 49 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)የአሳፍ መዝሙር። 1 የአማልክት አምላክ እግዚአብሔር ተናገረ፥ ምድርንም ጠራት፤ ከፀሐይ መውጫ ጀምሮ እስከ መግቢያዋ ድረስ። 2 ከክብሩ ውበት ከጽዮንም፥ 3 እግዚአብሔር በግልጥ ይመጣል። አምላካችንም ዝም አይልም፤ እሳት በፊቱ ይነድዳል፥ በዙሪያውም ብዙ ዐውሎ አለ። 4 በላይ ያለውን ሰማይን ምድርንም በሕዝቡ ለመፍረድ ይጠራል፥ 5 እንደ ሕጉ መሥዋዕትን የሚያቀርቡትን፥ ጻድቃኑን ሰብስቡለት። 6 ሰማያት ጽድቁን ይናገራሉ፥ እግዚአብሔር ፈራጅ ነውና። 7 ሕዝቤ፥ ስማኝ ልንገርህ፤ እስራኤልም እመሰክርብሃለሁ፤ አምላክስ እኔ አምላክህ ነኝ። 8 ስለ መሥዋዕትህ የምዘልፍህ አይደለሁም፤ የሚቃጠል ቍርባንህም ሁልጊዜ በፊቴ ነው። 9 ከቤትህ ፍሪዳን፥ ከመንጋህም ጊደርን አልወስድም፤ 10 የዱር አራዊት ሁሉ፥ የምድረ በዳ እንስሶችና ላሞች ሁሉ የእኔ ናቸውና። 11 የሰማይን አዕዋፍ ሁሉ አውቃለሁ፥ የዱር ውበትም በእኔ ዘንድ አለ። 12 ብራብም አልለምንህም፥ ዓለም ሁሉ በመላው የእኔ ነውና። 13 የፍሪዳውን ሥጋ አልበላም፥ የፍየሉንም ደም አልጠጣም። 14 ለእግዚአብሔር የምስጋናን መሥዋዕት ሠዋ፥ ለልዑልም ጸሎትህን ስጥ፤ 15 በመከራህ ቀን ትጠራኛለህ አድንህማለሁ፥ አንተም ታከብረኛለህ። 16 ኀጢአተኛውን ግን እግዚአብሔር አለው፦ “ለምን አንተ ሕጌን ትናገራለህ? ኪዳኔንም በአፍህ ለምን ትወስዳለህ? 17 አንተስ ተግሣጼን ጠላህ፥ ቃሌንም ወደ ኋላህ መለስኽ። 18 ሌባውን ባየህ ጊዜ ከእርሱ ጋር ትሮጣለህ፥ ዕድል ፋንታህንም ከአመንዝሮች ጋር አደረግህ። 19 አፍህ ክፋትን አበዛች፥ አንደበትህም ሽንገላን ተበተባት። 20 ተቀምጠህ ወንድምህን ታማዋለህ፥ ለእናትህም ልጅ ዕንቅፋትን አኖርህ። 21 ይህን አድርገህ ዝም አልሁህ፤ ኀጢአት አማረችህን? እኔ እንዳንተ እሆን ዘንድ ጠረጠርህ? በፊትህ ቆሜ ልዝለፍህ? 22 እግዚአብሔርን የምትረሱ እናንተ፥ ይህን አስተውሉ፤ አለዚያ ግን ይነጥቃል፥ የሚያድንም የለም። 23 የከበረች መሥዋዕት ታከብረኛለች፥ እግዚአብሔር ማዳኑን ያሳየባት መንገድ በዚያ አለች።” |