መዝሙር 43 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)ለመዘምራን አለቃ የቆሬ ልጆች ትምህርት። 1 አቤቱ፥ በጆሮአችን ሰማን፥ አባቶቻችንም በዘመናቸው በቀድሞ ዘመን የሠራኸውን ሥራ ነገሩን። 2 እጅህ ጠላትን አጠፋች፥ እነርሱንም ተከልህ፤ አሕዛብን አሠቃየኻቸው፥ አሳደድኻቸውም። 3 በጦራቸው ምድርን አልወረሱም፥ ክንዳቸውም አላዳናቸውም፤ ቀኝህና ክንድህ የፊትህም ብርሃን ነው እንጂ፤ ይቅር ብለሃቸዋልና። 4 አምላኬና ንጉሤ አንተ ነህ፤ ለያዕቆብ መድኀኒትን ያዘዝህ። 5 በአንተ ጠላቶቻችንን ሁሉ እንወጋቸዋለን፥ በስምህም በላያችን የቆሙትን እናዋርዳቸዋለን። 6 በቀስቴ የምታመን አይደለሁም፥ ጦሬም አያድነኝም፤ 7 አንተ ግን ከከበቡን አዳንኸን፥ የሚጠሉንንም ሁሉ አሳፈርሃቸው። 8 ሁልጊዜ በእግዚአብሔር እንከብራለን፥ ስምህንም ለዘለዓለም እናመሰግናለን። 9 አሁን ግን ጣልኸን፥ አሳፈርኸንም፥ አምላካችን፥ ከሠራዊታችን ጋር አትወጣም። 10 በጠላቶቻችን ዘንድ ወደ ኋላችን መለስኸን፥ ጠላቶቻችንም ተነጣጠቁን። 11 እንደ በጎች ሊበሉን ሰጠኸን፥ ወደ አሕዛብም በተንኸን፥ 12 ሕዝብህን ያለ ዋጋ ሰጠህ፥ ለእልልታችንም ብዛት የለውም። 13 ለጎረቤቶቻችን ስድብ፥ በዙሪያችንም ላሉ መሣቂያና መዘበቻ አደረግኸን። 14 ለአሕዛብ ተረት፥ ለሕዝቡም የራስ መነቅነቂያ አደረግኸን። 15 እፍረቴ ሁልጊዜ በፊቴ ነው፥ እፍረት ፊቴን ሸፈነኝ። 16 ከሚሳደብና ከሚላገድ ቃል የተነሣ፥ ከሚከብብ ጠላት ፊት የተነሣ ነው። 17 ይህ ሁሉ በእኛ ላይ ደረሰ፥ አልረሳንህም፥ ኪዳንህንም አላፈረስንም። 18 ልባችንም ወደ ኋላው አልተመለሰም፥ ፍለጋችንም ከመንገድህ ፈቀቅ አላለም፤ 19 በክፉ ስፍራ አዋርደኸናልና፥ የሞት ጥላም ሰውሮናልና፥ 20 የአምላካችንን ስም ረስተንስ ቢሆን፥ እጃችንንም ወደ ሌላ አምላክ አንሥተንስ ቢሆን፥ 21 እግዚአብሔር ይህን በተመራመረው ነበር! እርሱ ልባችን የሰወረውን ያውቃልና። 22 ስለ እርሱ ሁልጊዜ ይገድሉናልና፥ እንደሚታረዱም በጎች ሆነናል። 23 አቤቱ፥ ንቃ፤ ለምንስ ትተኛለህ? ተነሥ፥ ለዘወትርም አትጣለን። 24 ለምንስ ፊትህን ከእኛ ትመልሳለህ? መከራችንንና ችግራችንንስ ለምን ትረሳለህ? 25 ነፍሳችን በመሬት ላይ ተጐሳቍላለችና፥ ሆዳችንም ወደ ምድር ተጣብቃለችና። 26 አቤቱ፥ ተነሥና ርዳን፥ ስለ ስምህም ተቤዥን። |