መዝሙር 38 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)ለመዘምራን አለቃ ለኤዶታም የዳዊት መዝሙር። 1 “በአንደበቴ እንዳልስት አፌን እጠብቃለሁ፤ ኃጥኣን በፊቴ በተቃወሙኝ ጊዜ በአፌ ላይ ጠባቂ አኖራለሁ” አልሁ፤ 2 ዝም አልሁ ራሴንም አዋረድሁ፥ ለበጎ ነገርም ዝም አልሁ፥ ቍስሌም ታደሰብኝ። 3 ልቤም በውስጤ ሞቀብኝ፤ ከመናገሬም የተነሣ እሳት ነደደ፥ በአንደበቴም ተናገርሁ፦ 4 “አቤቱ፥ ፍጻሜዬን አስታውቀኝ” አልሁ፥ የዘመኔ ቍጥሮች ምን ያህል ናቸው? ዐውቅ ዘንድስ ለምን ወደ ኋላ እላለሁ? 5 እነሆ፥ ዘመኖቼን አስረጀሃቸው፤ አካሌም በፊትህ እንደ ኢምንት ነው። ነገር ግን የሰው ልጅ ሁሉ ከንቱ ነው። 6 ሰው ሁሉ እንደ ጥላ ይመላለሳል፥ ነገር ግን በከንቱ ይታወካሉ። ያከማቻሉ የሚሰበስቡለትንም አያውቁም። 7 አሁንስ ተስፋዬ ማን ነው? እግዚአብሔር አይደለምን? ትዕግሥቴም ከአንተ ዘንድ ነው። 8 ከኀጢአቴ ሁሉ አዳንኸኝ፥ ለሰነፎችም ስድብ አደረግኸኝ። 9 ዝም አልሁ አፌንም አልከፈትሁም። አንተ ፈጥረኸኛልና፤ 10 መቅሠፍትህን ከእኔ አርቅ፥ ከእጅህ ብርታት የተነሣ አልቄአለሁና። 11 በተግሣጽህ ስለ ኀጢአቱ ሰውን ዘለፍኸው፥ ሰውነቱንም እንደ ሸረሪት አቀለጥኻት፤ ነገር ግን ሰዎች ሁሉ በከንቱ ይታወካሉ። 12 አቤቱ፥ ጸሎቴን ስማ፥ ልመናዬንም አድምጥ፥ ልቅሶዬንም አድምጥ፥ ቸልም አትበለኝ፤ እኔ በምድር ላይ መጻተኛ ነኝና፥ እንደ አባቶችም ሁሉ እንግዳ ነኝና። 13 ወደማልመለስበት ሳልሄድ ዐርፍ ዘንድ ተወኝ። |