መዝሙር 29 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)ለቤቱ መመረቅ ምስጋና የዳዊት መዝሙር። 1 አቤቱ፥ ተቀብለኸኛልና፥ የጠላቶቼ መዘባበቻ አላደረግኸኝምና አመሰግንሃለሁ። 2 አቤቱ አምላኬ፥ ወደ አንተ ጮኽሁ፥ ይቅርም አልኸኝ። 3 አቤቱ፥ ነፍሴን ከሲኦል አወጣሃት፥ ወደ ጕድጓድም ከሚወርዱት ለይተህ አዳንኸኝ። 4 ጻድቃን ሆይ፥ ለእግዚአብሔር ዘምሩ፥ ለቅድስናውም መታሰቢያ አመስግኑ። 5 መቅሠፍቱ ከቍጣው ነውና፥ መዳንም ከፈቃዱ ነውና፤ ማታ ልቅሶ ይሰማል፥ ጥዋት ግን ደስታ ይሆናል። 6 እኔም በደስታዬ፥ “ለዘለዓለም አልታወክም” አልሁ። 7 አቤቱ፥ በፈቃድህ ለሕይወቴ ኀይልን ስጣት፤ ፊትህን መለስህ፥ እኔም ደነገጥሁ። 8 አቤቱ፥ ወደ አንተ ጮኽሁ፥ ወደ አምላኬም ለመንሁ። 9 ወደ ጥፋት ብወርድ በደሜ ምን ጥቅም አለ? አፈር ያመሰግንሃልን? ጽድቅህንም ይናገራልን? 10 እግዚአብሔር ሰማ፥ ይቅርም አለኝ፤ እግዚአብሔር ረዳቴ ሆነኝ። 11 ልቅሶዬን መልሰህ ደስ አሰኘኸኝ። ማቄን ቀድደህ ደስታን አስታጠቅኸኝ። 12 ክብሬ እንዲዘምርልህ እንዳልደነግጥም፥ አቤቱ፥ አምላኬ ለዘለዓለም አመሰግንሃለሁ። |