መዝሙር 137 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)የሐጌና የዘካርያስ የዳዊት መዝሙር። 1 አቤቱ፥ በፍጹም ልቤ አመሰግንሃለሁ፥ የአፌን ነገር ሁሉ ሰምተኸኛልና፤ በመላእክት ፊት እዘምርልሃለሁ። 2 በቤተ መቅደስህም እሰግዳለሁ፤ ስለ ምሕረትህና ስለ እውነትህም ስምህን አመሰግናለሁ፥ በሁሉ ላይ ቅዱስ ስምህን ከፍ ከፍ አድርገሃልና። 3 በጠራሁህ ቀን በፍጥነት አድምጠኝ፤ ነፍሴን በኀይልህ በብዙ አጸናሃት። 4 አቤቱ፥ የምድር ነገሥታት ሁሉ ያመሰግኑሃል፤ የአፍህን ቃል ሁሉ ሰምተዋልና። 5 በእግዚአብሔርም ምስጋና ይዘምራሉ። የእግዚአብሔር ክብር ታላቅ ነውና። 6 እግዚአብሔር ከፍ ያለ ነውና፥ የተዋረዱትንም ይመለከታልና፤ ትቢተኛውንም ከሩቁ ያውቀዋል። 7 በመከራ መካከል እንኳ ብሄድ፥ አንተ ታድነኛለህ፤ በጠላቶች ቍጣ ላይ እጆችህን ትዘረጋለህ፥ ቀኝህም ያድነኛል 8 እግዚአብሔርም ይበቀልልኛል፤ አቤቱ፥ ምሕረትህ ለዘለዓለም ነው፤ አቤቱ የእጅህን ሥራ ቸል አትበል። |