መዝሙር 117 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)ሃሌ ሉያ። 1 እግዚአብሔርን አመስግኑ፥ ቸር ነውና፥ ምሕረቱ ለዘለዓለም ነውና። 2 ቸር እንደ ሆነ፥ ምሕረቱ ለዘለዓለም እንደ ሆነ፥ የእስራኤል ወገን ንገሩ። 3 ቸር እንደ ሆነ፥ ምሕረቱ ለዘለዓለም እንደ ሆነ፥ የአሮን ወገን ንገሩ። 4 ቸር እንደ ሆነ፥ ምሕረቱ ለዘለዓለም እንደ ሆነ፥ እግዚአብሔርን የምትፈሩ ሁሉ ንገሩ። 5 በተጨነቅሁ ጊዜ እግዚአብሔርን ጠራሁት፤ ሰማኝ፥ አሰፋልኝም። 6 እግዚአብሔር ረዳቴ ነው፥ አልፈራም፤ ሰው ምን ያደርገኛል? 7 እግዚአብሔር ረዳቴ ነው፥ እነሆ፥ በጠላቶቼ ላይ አያለሁ። 8 በሰው ከመታመን በእግዚአብሔር መታመን ይሻላል። 9 በአለቆች ተስፋ ከማድረግ ይልቅ በእግዚአብሔር ተስፋ ማድረግ ይሻላል። 10 አሕዛብ ሁሉ ከበቡኝ፥ በእግዚአብሔርም ስም አሸነፍኋቸው፤ 11 መክበቡንስ ከበቡኝ፥ በእግዚአብሔርም ስም አሸነፍኋቸው፤ 12 ንብ ማርን እንደሚከብብ ከበቡኝ፥ እሳትም በእሾህ ውስጥ እንደሚነድድ ነደዱ፤ በእግዚአብሔርም ስም አሸነፍኋቸው። 13 ለመውደቅም ተንገደገድሁ፤ እግዚአብሔር ግን አነሣኝ። 14 ኀይሌም ስም አጠራሬም እግዚአብሔር ነው፥ እርሱም አዳኜ ሆነኝ። 15 የደስታ ድምፅ በጻድቃን ማደሪያዎች ነው የእግዚአብሔር ቀኝ ኀይልን አደረገች። 16 የእግዚአብሔር ቀኝ ከፍ ከፍ አደረገችኝ፤ የእግዚአብሔር ቀኝ ኀይልን አደረገች። 17 አልሞትም በሕይወት እኖራለሁ እንጂ፥ የእግዚአብሔርንም ሥራ እናገራለሁ። 18 መገሠጽስ እግዚአብሔር ገሠጸኝ፤ ለሞት ግን አሳልፎ አልሰጠኝም። 19 የጽድቅን ደጆች ክፈቱልኝ፤ ወደ እነርሱ ገብቼ እግዚአብሔርን አመሰግን ዘንድ። 20 ይህች የእግዚአብሔር ደጅ ናት፤ ወደ እርስዋ ጻድቃን ይገባሉ። 21 ሰምተኸኛልና፥ አዳኜም ሆነኸኛልና አቤቱ፥ አመሰግንሃለሁ። 22 ግንበኞች የናቋት ድንጋይ፥ እርሷ የማዕዘን ራስ ሆነች፥ 23 ይህች ከእግዚአብሔር ዘንድ ሆነች፥ ለዐይኖቻችንም ድንቅ ናት። 24 እግዚአብሔር የሠራት ቀን ይህች ናት፤ በእርስዋ ደስ ይበለን፥ ሐሤትንም እናድርግባት። 25 አቤቱ፥ እባክህ፥ አሁን አድን፤ አቤቱ፥ እባክህ፥ አሁን አቅና። 26 በእግዚአብሔር ስም የሚመጣ ቡሩክ ነው፤ ከእግዚአብሔር ቤት መረቅናችሁ። 27 ጌታ እግዚአብሔር ተገለጠልን፤ እስከ መሠዊያው ቀንዶች ድረስ በሚያስተነትኑበት በደስታ በዓልን አድርጉ። 28 አንተ አምላኬ ነህ፥ አመሰግንህማለሁ። አንተ አምላኬ ነህ፥ ከፍ ከፍም አደርግሃለሁ፤ ሰምተኸኛልና፥ አዳኜም ሆነኸኛልና አመሰግንሃለሁ። 29 እግዚአብሔርን አመስግኑ፥ ቸር ነውና፥ ምሕረቱ ለዘለዓለም ነውና። |