መዝሙር 113 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)ሃሌ ሉያ። 1 እስራኤል ከግብፅ፥ የያዕቆብም ወገን ከጠላት ሕዝብ በወጡ ጊዜ፥ 2 ይሁዳ መመስገኛው፥ እስራኤልም ግዛቱ ሆነ። 3 ባሕር አየች፥ ሸሸችም፥ ዮርዳኖስም ወደኋላው ተመለሰ። 4 ተራሮች እንደ ኮርማዎች፥ ኮረብቶችም እንደ በጎች ጠቦቶች ዘለሉ። 5 አንቺ ባሕር የሸሸሽ፥ አንተም ዮርዳኖስ ወደ ኋላህ የተመለስህ፥ ምን ሁናችሁ ነው? 6 እናንተም ተራሮች፥ እንደ ኮርማዎች፥ ኮረብቶችስ፥ እንደ በጎች ጠቦቶች ለምን ዘለላችሁ? 7 ከያዕቆብ አምላክ ፊት፥ ከእግዚአብሔር ፊት ምድር ተናወጠች፤ 8 ዐለቱን ወደ ውኃ ምንጭ፥ ባልጭቱንም ወደ ውኃ ኩሬ የለወጠ። 9 ለእኛ አይደለም፥ አቤቱ፥ ለእኛ አይደለም፥ ነገር ግን ለስምህ፥ ስለ ምሕረትህና ስለ እውነትህም ምስጋናን እንስጥ 10 አሕዛብ፥ “አምላካቸው ወዴት ነው?” አይበሉ። 11 አምላካችንስ በላይ በሰማይ ነው፤ በሰማይም በምድርም፥ እግዚአብሔር የፈቀደውን ሁሉ አደረገ። 12 የአሕዛብ ጣዖታቶች የወርቅና የብር፥ የሰው እጅ ሥራ ናቸው። 13 አፍ አላቸው ግን አይናገሩም፤ ዐይን አላቸው ግን አያዩም፤ 14 ጆሮ አላቸው ግን አይሰሙም፤ አፍንጫ አላቸው ግን አያሸትቱም፤ 15 እጅ አላቸው ግን አይዳስሱም፤ እግር አላቸው ግን አይሄዱም፤ በጉሮሮአቸውም አይናገሩም። 16 በአፋቸው ትንፋሽ የለም፥ የሚሠሩአቸውም የሚያምኑባቸውም ሁሉ እንደ እነርሱ ይሁኑ። 17 የእስራኤል ወገኖች ሆይ፥ በእግዚአብሔር ታመኑ፤ ረዳታቸውና መታመኛቸው እርሱ ነው። 18 የአሮን ወገኖች ሆይ፥ በእግዚአብሔር ታመኑ፤ ረዳታቸውና መታመኛቸው እርሱ ነው። 19 እግዚአብሔርን የምትፈሩ ሆይ፥ በእግዚአብሔር ታመኑ፤ ረዳታቸውና መታመኛቸው እርሱ ነው። 20 እግዚአብሔር ሆይ፥ አስበን ባርከንም የእስራኤልንም ወገኖች ባርክ፥ የአሮንንም ወገኖች ባርክ። 21 እግዚአብሔርን የሚፈሩትን፥ ትንንሾችንና ትልልቆችን ሁሉ ባርካቸው። 22 እግዚአብሔር በላያችሁ፥ በላያችሁና በልጆቻችሁ ላይ ይጨምር። 23 እናንተ ሰማይንና ምድርን ለሠራ ለእግዚአብሔር የተባረካችሁ ናችሁ። 24 የሰማዮች ሰማይ ለእግዚአብሔር ነው፤ ምድርን ግን ለሰው ልጆች ሰጠ። 25 አቤቱ፥ ሙታን የሚያመሰግኑህ አይደሉም፥ ወደ ሲኦልም የሚወርዱ ሁሉ፤ 26 እኛ ሕያዋን ግን ከዛሬ ጀምሮ እስከ ዘለዓለም እግዚአብሔርን እናመሰግናለን። |