ዘኍል 31 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)በምድያማውያን ላይ የተደረገ ጦርነት ( ዘዳ. 3፥12-22 ) 1 እግዚአብሔርም ሙሴን እንዲህ ብሎ ተናገረው፦ 2 “የእስራኤልን ልጆች በቀል ምድያማውያንን ተበቀል፤ ከዚያም በኋላ ወደ ወገኖችህ ትጨመራለህ።” 3 ሙሴም ለሕዝቡ እንዲህ ብሎ ነገራቸው፥ “ከእናንተ መካከል ሰዎችን አስታጥቁ፤ ከእግዚአብሔር ዘንድ ምድያምን ይበቀሉ ዘንድ በእግዚአብሔር ፊት ከምድያም ጋር ይሰለፉ። 4 ከእስራኤል ነገዶች ሁሉ ከየነገዱ አንድ አንድ ሺህ ሰው ወደ ጦርነት ስደዱ፤” 5 ከእስራኤልም አእላፋት፥ ከየነገዱ አንድ አንድ ሺህ ቈጠሩ፤ ለጦርነት የተሰለፉትም ዐሥራ ሁለት ሺህ ሆኑ። 6 ሙሴም ከየነገዱ አንድ ሺህ ከሠራዊታቸውና ከካህኑ ከአሮን ልጅ ከአልዓዛር ልጅ ከፊንሐስ ጋር ሰደደ፤ ንዋያተ ቅድሳቱና ምልክት መስጫ መለከቶችም በእጆቻቸው ነበሩ። 7 እግዚአብሔርም ሙሴን እንዳዘዘ ከምድያም ጋር ተዋጉ፤ ወንዶችንም ሁሉ ገደሉ። 8 የምድያምንም ነገሥታት በዚያው ጦርነት በአንድነት ገደሉአቸው፤ አምስቱም የምድያም ነገሥታት ኤዊ፥ ሮቆም፥ ሱር፥ ሑር፥ ሮባቅ ነበሩ፤ የቢዖርንም ልጅ በለዓምን ደግሞ በዚያው ጦርነት በሰይፍ ገደሉት። 9 የምድያምንም ሴቶችና ልጆቻቸውን ማረኩ፤ እንስሶቻቸውንና ዕቃቸውን፥ ንብረታቸውንና ኀይላቸውን በዘበዙ። 10 የተቀመጡባቸውን ከተሞቻቸውን ሁሉ፥ ሰፈሮቻቸውንም ሁሉ በእሳት አቃጠሉ። 11 ከሰው እስከ እንስሳ ምርኮአቸውንና ብዝበዛቸውን ሁሉ ወሰዱ። 12 የማረኩትን ምርኮውንና የዘረፉትን ወደ ሙሴና ወደ ካህኑ ወደ አልዓዛር፥ ወደ እስራኤልም ልጆች፥ በዮርዳኖስም አጠገብ በኢያሪኮ ፊት ለፊት በሞዓብ ሜዳ ወዳለው ሰፈር አመጡ። የሠራዊቱ ከጦርነት መመለስ 13 ሙሴና ካህኑ አልዓዛርም፥ የማኅበሩም አለቆች ሁሉ ከሰፈሩ ወደ ውጭ ሊገናኙአቸው ወጡ። 14 ሙሴም ከዘመቻ በተመለሱት በጭፍራ አለቆች፥ በሻለቆችና በመቶ አለቆች ላይ ተቈጣ። 15 ሙሴም አላቸው፥ “ሴቶችን ሁሉ ለምን አዳናችኋቸው? 16 እነርሱ በበለዓም ምክር በፌጎር ምክንያት የእስራኤልን ልጆች የሚያስቱ፥ የእግዚአብሔርንም ቃል እንዲስቱ የሚያደርጉ ዕንቅፋቶች ናቸውና፤ ስለዚህም በእግዚአብሔር ማኅበር ላይ መቅሠፍት ሆኖአል፤ 17 አሁንም እንግዲህ ወንዱን ሁሉ በአለበት ግደሉ፥ ወንድንም የምታውቀውን ሴት ሁሉ ግደሉ። 18 ወንድን የማያውቁትን ሴቶች ልጆችን ሁሉ ግን አድኑአቸው። 19 እናንተም ከሰፈሩ ውጭ ሰባት ቀን ስፈሩ፤ ሰውን የገደለ ሁሉ፥ የተገደለውንም የዳሰሰ ሁሉ፥ እናንተና የማረካችኋቸውም በሦስተኛውና በሰባተኛው ቀን ሰውነታችሁን ንጹሕ አድርጉ። 20 ልብስንም፥ ከቁርበትም የተዘጋጀውን ሁሉ፥ ከፍየልም ጠጕር፥ ከዕንጨትም የተሠራውን ሁሉ ንጹሕ አድርጉ።” 21 ካህኑም አልዓዛር ከሰልፍ የመጡትን ሰዎች አላቸው፥ “እግዚአብሔር ሙሴን ያዘዘው የሕጉ ሥርዐት ይህ ነው፤ 22 ወርቁና ብሩ፥ ናሱም፥ ብረቱም፥ ቆርቆሮውም፥ እርሳሱም፥ 23 በእሳት ለማለፍ የሚችለው ነገር ሁሉ፥ ንጹሕ ይሆናል፤ ነገር ግን በማንጻት ውኃ ደግሞ ይጠራል። በእሳትም ለማለፍ የማይችለውን በውኃ ታሳልፉታላችሁ። 24 በሰባተኛውም ቀን ልብሳችሁን እጠቡ፤ ንጹሓንም ትሆናላችሁ፤ ከዚያም በኋላ ወደ ሰፈሩ ትቀርባላችሁ።” ምርኮ እንደ ተካፈሉ 25 እግዚአብሔርም ሙሴን እንዲህ ብሎ ተናገረው፦ 26 “አንተና ካህኑ አልዓዛር፥ የማኅበሩም አባቶች አለቆች የተማረኩትን ሰውና እንስሳ ቍጠሩ። 27 ምርኮውንም በተዋጉትና ወደ ሰልፍ በወጡት፥ በማኅበሩም ሁሉ መካከል ትከፍላላችሁ። 28 ከእነዚያም ከተዋጉት፥ ወደ ሰልፍም ከወጡት ሰልፈኞች ዘንድ ከሰዎችም፥ ከበሬዎችም፥ ከበጎችም፥ ከአህዮችም፥ ከአምስት መቶ አንድ ለእግዚአብሔር ግብር ታወጣላችሁ። 29 ከድርሻቸው እኩሌታ ወስደህ የእግዚአብሔርን ቀዳምያት ለካህኑ ለአልዓዛር ትሰጠዋለህ። 30 ከእስራኤልም ልጆች ድርሻ እኩሌታ፥ ከሰዎችም፥ ከበሬዎችም፥ ከበጎችም፥ ከአህዮችም፥ ከእንስሶችም ሁሉ ከአምሳ አንድ ትወስዳለህ፤ የእግዚአብሔርንም ድንኳን ሥርዐት ለሚጠብቁ ለሌዋውያን ትሰጣለህ።” 31 ሙሴና ካህኑ አልዓዛርም እግዚአብሔር ሙሴን እንዳዘዘው አደረጉ። 32 ወደ ሰልፍ የወጡ ሰዎችም ከወሰዱት ብዝበዛ የቀረው ምርኮ እንዲህ ሆነ፤ ስድስት መቶ ሰባ አምስት ሺህ በጎች፤ 33 ሰባ ሁለት ሺህ በሬዎች፥ 34 ስድሳ አንድ ሺህ አህዮች፥ 35 ወንድ ከማያውቁ ሴቶችም ሠላሳ ሁለት ሺህ ነፍስ። 36 በዘመቻም ለነበሩ ሰዎች ድርሻ የሆነ እኩሌታ ከበግ ሦስት መቶ ሠላሳ ሰባት ሺህ አምስት መቶ በጎች ነበሩ፤ 37 ከበጎችም የእግዚአብሔር ግብር ስድስት መቶ ሰባ አምስት ነበረ። 38 በሬዎችም ሠላሳ ስድስት ሺህ ነበሩ፤ የእግዚአብሔርም ግብር ሰባ ሁለት ነበረ። 39 አህዮቹም ሠላሳ ሺህ አምስት መቶ ነበሩ፤ የእግዚአብሔርም ግብር ስድሳ አንድ ነበረ። 40 ሰዎቹም ዐሥራ ስድስት ሺህ ነበሩ ፤ የእግዚአብሔርም ግብር ሠላሳ ሁለት ነበረ። 41 እግዚአብሔርም ሙሴን እንዳዘዘው ሙሴ፦ ለእግዚአብሔር የለዩትን ግብር ለካህኑ ለአልዓዛር ሰጠው። 42 ከእስራኤል ልጆች እኩሌታም፥ ወደ ሰልፍ ከወጡት ወንዶች ላይ ሙሴ የለየው፥ 43 የማኅበሩ ድርሻ ሦስት መቶ ሠላሳ ሰባት ሺህ አምስት መቶ በጎች፥ 44 ሠላሳ ስድስት ሺህ በሬዎች፤ 45 ሠላሳ ሺህ አምስት መቶ አህዮች፥ 46 ዐሥራ ስድስት ሺህ ሰዎች ነበሩ። 47 ሙሴ ከእስራኤል ልጆች ድርሻ ከሰውና ከእንስሳ ከሃምሳ አንድ ወሰደ፤ እግዚአብሔርም ሙሴን እንዳዘዘው የእግዚአብሔርን ድንኳን ሥርዐት ለሚጠብቁ ሌዋውያን ሰጠ። 48 በሠራዊት አእላፋት ላይ የተሾሙት አለቆች፥ ሻለቆችና የመቶ አለቆች ወደ ሙሴ ቀረቡ፤ ሙሴንም እንዲህ አሉት፦ 49 “ባሪያዎችህ ወደ ሰልፍ የወጡትን ከእጃችን በታች ያሉትን ቈጠሩ፤ ከእኛም አንድ አልጐደለም። 50 ሰውም ሁሉ ከአገኘው ከወርቅ ዕቃ፥ ከእግር አልቦም፥ ከአምባርም፥ ከቀለበትም ከጕትቻም፥ ከድሪውም ስለ እኛ በእግዚአብሔር ፊት ታስተሰርዩልን ዘንድ ለእግዚአብሔር መባ አምጥተናል” አሉት። 51 ሙሴና ካህኑ አልዓዛርም ወርቁንና በልዩ ልዩ የተሠራውን ዕቃ ሁሉ ከእጃቸው ተቀበሉ። 52 ከሻለቆችና ከመቶ አለቆች ለእግዚአብሔር የለዩትና ያቀረቡት ወርቅ ሁሉ ዐሥራ ስድስት ሺህ ሰባት መቶ አምሳ ሰቅል ነበረ። 53 ወደ ሰልፍ የወጡ ሰዎች ሁሉ የማረኩትን ለየራሳቸው ወሰዱ። 54 ሙሴና ካህኑ አልዓዛርም ወርቁን ከሻለቆችና ከመቶ አለቆች ወሰዱ፤ በእግዚአብሔርም ፊት ለእስራኤል ልጆች መታሰቢያ ወደ ምስክሩ ድንኳን አገቡት። |