ዘኍል 19 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)በሐመደ ዕጐልት የሚፈጸም የኀጢአት ስርየት ሥርዐት 1 እግዚአብሔርም ሙሴንና አሮንን እንዲህ ብሎ ተናገራቸው፦ 2 “እግዚአብሔር ያዘዘው የሕጉ ትእዛዝ ይህ ነው፤ መልካሚቱን፥ ነውርም የሌለባትን፥ ቀንበርም ያልተጫነባትን ቀይ ጊደር ያመጡልህ ዘንድ ለእስራኤል ልጆች ንገራቸው። 3 እርስዋንም ለካህኑ ለአልዓዛር ትሰጠዋለህ፤ ከሰፈር ወደ ውጭ ወደ ንጹሕ ስፍራ ይወስዷታል፤ በፊቱም ያርዷታል። 4 አልዓዛርም ከደምዋ በጣቱ ይወስዳል፤ ከደምዋም ወደ ምስክሩ ድንኳን ፊት ሰባት ጊዜ ይረጫል። 5 ጊደሪቱንም በፊቱ ያቃጥሏታል፤ ቍርበቷንም፥ ሥጋዋንም፥ ደምዋንም፥ ፈርስዋንም ያቃጥሉት። 6 ካህኑም የዝግባ ዕንጨት ሂሶጵም፥ ቀይ ግምጃም ወስዶ ጊደሪቱ በምትቃጠልበት እሳት መካከል ይጥለዋል። 7 ካህኑም ልብሱን ያጥባል፤ ገላውንም በውሃ ይታጠባል፤ ከዚያም በኋላ ወደ ሰፈሩ ይገባል፤ ካህኑም እስከ ማታ ርኩስ ይሆናል። 8 ያቃጠላትም ሰው ልብሱን በውሃ ያጥባል፤ ገላውንም በውኃ ይታጠባል፤ እስከ ማታም ድረስ ርኩስ ይሆናል። 9 ንጹሕም ሰው የጊደሪቱን አመድ ያከማቻል፤ ከሰፈሩም ውጭ በንጹሕ ስፍራ ያኖረዋል፤ ርኵሰት ለሚያነጻ ውኃ ለእስራኤል ልጆች ማኅበር ይጠበቃል፤ ይነጹበታልና። 10 የጊደሪቱንም አመድ ያከማቸው ሰው ልብሱን ያጥባል፤ ገላውንም ይታጠባል፤ እስከ ማታም ድረስ ርኩስ ይሆናል፤ ይህም ለእስራኤል ልጆች በመካከላቸውም ለሚኖር መጻተኛ ለዘለዓለም ሥርዐት ይሆናል። በድን የሚነካ ስለሚነጻበት ሕግ 11 “የሞተውን ሰው በድን የሚነካ ሰባት ቀን ርኩስ ይሆናል። 12 እንደዚሁ በሦስተኛውና በሰባተኛው ቀን ሁለመናውን ያነጻል፤ ንጹሕም ይሆናል፤ ነገር ግን በሦስተኛውና በሰባተኛው ቀን ሁለመናውን ባያነጻ ንጹሕ አይሆንም። 13 የሞተውን ሰው በድን የነካ ሁለመናውን ባያነጻ የእግዚአብሔርን ድንኳን ያረክሳል፤ ያ ሰው ከእስራኤል ዘንድ ተለይቶ ይጠፋል፤ በእርሱም ላይ የሚያነጻ ውኃ አልተረጨምና ርኩስ ይሆናል፤ ርኵሰቱ ገና በእርሱ ላይ ነው። 14 “ሰው በቤት ውስጥ ቢሞት ሕጉ ይህ ነው፤ ወደ ቤት የሚገባ ሁሉ በቤቱም ውስጥ ያለው ሁሉ ሰባት ቀን ርኩስ ይሆናል። 15 መክደኛው ያልታሰረ የተከፈተ ዕቃ ሁሉ ርኩስ ነው። 16 በሜዳም የተገደለውን ወይም የሞተውን በድን፥ ወይም የሰውን አጥንት፥ ወይም መቃብር የሚነካ ሰባት ቀን ርኩስ ይሆናል። 17 ለአንጽሖ እንድትሆን ከተቃጠለችው ጊደር አመድ ለርኩሱ ይወስዱለታል፤ በዕቃውም ውስጥ የምንጭ ውኃ ይቀላቅሉበታል። 18 ንጹሕም ሰው ሂሶጱን ወስዶ በውኃው ውስጥ ያጠልቀዋል፤ በቤቱም፥ በዕቃውም ሁሉ፥ በዚያም ባሉ ሰዎች ላይ፥ አጥንቱንም ወይም የተገደለውን፥ ወይም የሞተውን፥ ወይም መቃብሩን በነካው ላይ ይረጨዋል። 19 ንጹሑም በሦስተኛው ቀንና በሰባተኛው ቀን በርኩሱ ላይ ይረጨዋል፤ በሰባተኛውም ቀን ይነጻል፤ እርሱም ልብሱን ያጥባል፤ ገላውንም በውኃ ይታጠባል፥ እስከ ማታም ርኩስ ነው። 20 “ሰውም ርኩስ ቢሆን ሁለመናውንም ባያነጻ፥ ያ ሰው የእግዚአብሔርን መቅደስ አርክሶአልና ከማኅበሩ መካከል ተለይቶ ይጠፋል፤ በሚያነጻ ውኃ አልተረጨምና ርኩስ ነው። 21 ይህ የዘለዓለም ሥርዐት ይሆንላችኋል፤ የሚያነጻውን ውኃ የሚረጭ ሰው ልብሱን ያጥባል፤ የሚያነጻውንም ውኃ የሚነካ እስከ ማታ ድረስ ርኩስ ይሆናል። 22 ርኩሱም የሚነካው ነገር ሁሉ ርኩስ ይሆናል፤ የሚነካውም ሰው እስከ ማታ ድረስ ርኩስ ይሆናል።” |