ኢዮብ 4 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)የኤልፋዝ ንግግር 1 ቴማናዊውም ኤልፋዝ መለሰ፥ እንዲህም አለ፦ 2 “በመከራ ሳለህ ነገር አታብዛ፥ የነገር ብዛት ምን ይጠቅምሃል? 3 እነሆ፥ አንተ ብዙዎችን ታስተምር ነበር፥ የደከሙትንም እጆች ታበረታ ነበር፥ 4 በቃልህ በሽተኞችን ታስነሣ ነበር፥ የሚብረከረከውንም ጕልበት ታጸና ነበር። 5 አሁን ግን ሕማም በአንተ ላይ መጥቶ ዳሰሰህ። አንተም ተቸገርህ። 6 ጥንቱን ፍርሀትህ፥ ተስፋህም፥ የመንገድህም ጠማማነት፥ ስንፍና አይደለምን? 7 እባክህ አስብ፥ ንጹሕ ሆኖ የጠፋ ማን ነው? ከጻድቃንስ የተደመሰሰ ማን ነው? 8 እኔ እንዳየሁ፥ ኀጢኣትን የሚያርሱ፥ የሚዘሩአትም መከራን ለራሳቸው ያጭዳሉ። 9 በእግዚአብሔርም ትእዛዝ ይጠፋሉ፥ በቍጣውም መንፈስ ያልቃሉ። 10 የአንበሳው ጩኸት፥ የአንበሳዪቱም ድምፅ፥ የእባቦችም አስፈሪ ጩኸት ጠፉ። 11 “ገብረ ጉንዳን ምግብ በማጣት አለቀ፥ የአንበሳዪቱ ግልገሎችም እርስ በእርሳቸው ተላለቁ። 12 ነገር ግን አንተ አንዳች እውነት አድርገህ ቢሆን ኖሮ፥ ይህ ሁሉ ባልደረሰብህም ነበር። በእኔ ዘንድ ነገር ይነሣል፤ ዦሮዬም ከእርሱ ድምፅን ትሰማለች፤ ጥንቱን የነገረኝን አላምነውምን? 13 በሰዎች ላይ ፍርሀት በወደቀ ጊዜ በሌሊት ከፍርሀትና ከድምፅ ጋር 14 ድንጋጤና መንቀጥቀጥ ያዙኝ፤ አጥንቶቼም ሁሉ እጅግ ተነዋወጡ፤ 15 መንፈሴም በፊቴ ዐለፈ፥ ሥጋዬም፥ ጠጕሬም ተቈጣ። 16 ተነሣሁ፤ ነገር ግን አላወቅሁም፥ ተመለከትሁ፥ በዐይኖቼም ፊት መልክ አልነበረም። ነገር ግን ጥላን አያለሁ፤ ድምፅንም እሰማለሁ፦ 17 በእግዚአብሔር ፊት ንጹሕ የሚሆን ሟች ማን ነው? በሥራውስ የሚጸድቅ ሰው ማን ነው? 18 እነሆ፥ አገልጋዮቹንም አይተማመናቸውም፥ መላእክቱንም በጭንቅ ይጠራጠራቸዋል። 19 ይልቁንም ከአንድ ዐይነት ጭቃ የተፈጠርን እኛ፥ በተፈጠርንበት የጭቃ ቤት የሚኖሩትን እንደ ብል ይጨፈልቃቸዋል። 20 ከጥዋት እስከ ማታ አይኖሩም። ራሳቸውን ማዳንና መርዳት አይችሉምና ጠፉ። 21 እፍ ብሎባቸዋልና ይደርቃሉ፥ ጥበብም የላቸውምና ይጠፋሉ። |