ኤርምያስ 43 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)ኤርምያስ ወደ ግብፅ እንደ ተወሰደ 1 የአምላካቸውን የእግዚአብሔርን ቃል ሁሉ፥ ለእነርሱ አምላካቸው እግዚአብሔር የላከውን ይህን ቃል ሁሉ፥ ኤርምያስ ለሕዝቡ ሁሉ መናገርን በፈጸመ ጊዜ እንዲህ ሆነ፤ 2 የኢዮስያስ ልጅ ኣዛርያስ፥ የቃርሔም ልጅ ዮሐናን፥ ትዕቢተኞችም ሰዎች ሁሉ ኤርምያስን፥ “ሐሰት ተናግረሃል፤ አምላካችን እግዚአብሔር፦ በዚያ ትቀመጡ ዘንድ ወደ ግብፅ አትግቡ ብሎ አልላከህም፤ 3 ነገር ግን ከለዳውያን እንዲገድሉን ወደ ባቢሎንም እንዲያፈልሱን በእጃቸው አሳልፈህ ትሰጠን ዘንድ የኔርዩ ልጅ ባሮክ በላያችን ላይ አነሣሥቶሃል” አሉት። 4 የቃርሔም ልጅ ዮሐናን፥ የጭፍራ አለቆችም ሁሉ፥ ሕዝቡም ሁሉ በይሁዳ ምድር ይቀመጡ ዘንድ የእግዚአብሔርን ቃል አልሰሙም። 5 የቃርሔም ልጅ ዮሐናን፥ የጭፍራ አለቆችም ሁሉ በይሁዳ ምድር ለመቀመጥ ከተሰደዱባቸው ከአሕዛብ ሁሉ የተመለሱትን የይሁዳን ቅሬታ ሁሉ ወሰዱ። 6 ወንዶችንና ሴቶችን፥ ሕፃናቱንም፥ የንጉሡንም ሴቶች ልጆች፥ የአዛዦችም አለቃ ናቡዛርዳን ከሳፋን ልጅ ከአኪቃም ልጅ ከጎዶልያስ ጋር የተዋቸውን ሰዎች ሁሉ፥ ነቢዩ ኤርምያስንና የኔርዩን ልጅ ባሮክንም ወሰዱ። 7 የእግዚአብሔርንም ቃል አልሰሙምና ወደ ግብፅ ምድር ገቡ፤ እስከ ጣፍናስ ድረስም መጡ። 8 በጣፍናስም የእግዚአብሔር ቃል ወደ ኤርምያስ እንዲህ ሲል መጣ፦ 9 “ታላላቆችን ድንጋዮች በእጅህ ውሰድ፥ የይሁዳም ሰዎች እያዩ በጣፍናስ ባለው በፈርዖን ቤት ደጅ መግቢያ ሸሽጋቸው። 10 እንዲህም በላቸው፦ የእስራኤል አምላክ የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ እነሆ፥ ልኬ ባሪያዬን የባቢሎንን ንጉሥ ናቡከደነፆርን አመጣለሁ፤ ዙፋኑንም እኔ በሸሸግኋቸው በእነዚህ ድንጋዮች ላይ አኖራለሁ፤ ጋሻዎቹንም በእነርሱ ላይ ያነሣል። 11 መጥቶም የግብፅን ምድር ይመታል፤ ለሞትም የሚሆነውን ለሞት፥ ለምርኮም የሚሆነውን ለምርኮ፥ ለሰይፍም የሚሆነውን ለሰይፍ አሳልፎ ይሰጣል። 12 በግብፅም አማልክት ቤቶች እሳትን ያነድዳል፤ ያቃጥላቸውማል፤ ይማርካቸውማል፤ እረኛም ልብሱን እንደሚቀምል እንዲሁ የግብፅን ሀገር ይቀምላታል፤ ከዚያም በሰላም ይወጣል። 13 በግብፅ ምድርም ያለውን የፀሐይ ከተማ ምሰሶዎችን ይሰብራል፥ የግብፅንም አማልክት ቤቶች በእሳት ያቃጥላል።” |