ኤርምያስ 18 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)የሸክላውና የሸክላ ሠሪው ምሳሌ 1 ከእግዚአብሔር ዘንድ ወደ ኤርምያስ የመጣ ቃል፥ እንዲህም አለው፦ 2 “ተነሥተህ ወደ ሸክላ ሠሪው ቤት ውረድ፤ በዚያም ቃሌን አሰማሃለሁ።” 3 ወደ ሸክላ ሠሪውም ቤት ወረድሁ፤ እነሆም ሥራውን በዓለት ላይ ሲሠራ አገኘሁት። 4 ከጭቃም ይሠራው የነበረው ዕቃ ከሸክላ ሠሪው እጅ ወደቀ፤ ሸክላ ሠሪውም እንደ ወደደ ዳግመኛ ሌላ ዕቃ አድርጎ ሠራው። 5 የእግዚአብሔርም ቃል ወደ እኔ እንዲህ ሲል መጣ። 6 “የእስራኤል ቤት ሆይ! ይህ ሸክላ ሠሪ እንደሚሠራ በውኑ እኔ በእናንተ ዘንድ መሥራት አይቻለኝምን? እነሆ ጭቃው በሸክላ ሠሪ እጅ እንዳለ፥ እንዲሁ እናንተ በእኔ እጅ አላችሁ። 7 አጠፋቸውና እደመስሳቸው ዘንድ በሕዝብ ላይና በመንግሥት ላይ ቍርጥ ነገርን ተናገርሁ፤ 8 ስለ እነርሱ የተናገርሁባቸው ሕዝብ ከክፋታቸው ቢመለሱ፥ እኔ አደርግባቸው ዘንድ ካሰብሁት ክፉ ነገር እጸጸታለሁ። 9 በሕዝብም በመንግሥታትም ላይ እሠራቸውና እተክላቸው ዘንድ ቍርጥ ነገርን እናገራለሁ፤ 10 በፊቴ ክፉን ነገር ቢያደርጉ ቃሌንም ባይሰሙ፥ እኔ አደርግላቸው ዘንድ ስለ ተናገርሁት መልካም ነገር እጸጸታለሁ።” 11 አሁን እንግዲህ ለይሁዳ ሰዎችና በኢየሩሳሌም ለሚኖሩ፦ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፥ “እነሆ ክፉ ነገር እፈጥርባችኋለሁ፤ ምክርንም እመክርባችኋለሁ፤ አሁንም ሁላችሁ ከክፉ መንገዳችሁ ተመለሱ፤ መንገዳችሁንና ሥራችሁንም አቅኑ ብለህ ተናገራቸው።” 12 እነርሱ ግን፥ “እንጨክናለን፤ ክዳታችንን ተከትለን እንሄዳለን፥ ሁላችንም ክፉ ልባችንን ደስ የሚያሰኛትን እናደርጋለን” አሉ። 13 ስለዚህ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፥ “የእስራኤል ድንግል ያደረገችውን በጣም የሚያስደነግጠውን ነገር የሚሰሙት እንዳለ አሕዛብን ጠይቁ።” 14 ምንጭ ከዓለት ይጠፋልን? በረዶስ ከሊባኖስ ይጠፋልን? ወራጅ ውኃስ በኀይለኛ ነፋስ ይመለሳልን? 15 ሕዝቤ ግን ረስተውኛል፤ ለከንቱ ነገርም አጥነዋል፤ የቀድሞውን ጐዳና ትተው ወደ ጠማማውና ወደ ሰንከልካላው መንገድ ለመሄድ በመንገዳቸው ተሰናከሉ። 16 ምድራቸውን ለጥፋትና ለዘለዓለም ማፍዋጫ አድርገዋል፤ የሚያልፍባት ሁሉ ይደነቃል፤ ራሱንም ያነቃንቃል። 17 በጠላት ፊት እንደ በረሃ ዐውሎ ነፋስ እበትናቸዋለሁ፤ በጥፋታቸውም ቀን ጀርባዬን እንጂ ፊቴን አላሳያቸውም። በኤርምያስ ላይ የተደረገ ሴራ 18 እነርሱም፥ “ሕግ ከካህን፥ ምክርም ከጠቢብ፥ ቃልም ከነቢይ አይጠፋምና ኑ፤ በኤርምያስ ላይ ምክርን እንምከር። ኑ፤ በምላስ እንምታው፤ ቃሉንም ሁሉ አናዳምጥ” አሉ። 19 “አቤቱ! አድምጠኝ፤ የክርክሬንም ቃል ስማ። 20 ለሰውነቴ ጕድጓድን ቈፍረዋል፤ በውኑ በመልካም ፈንታ ክፉ ይመለሳልን? ስለ እነርሱ በመልካም እናገር ዘንድ፥ ቍጣህንም ከእነርሱ ትመልስ ዘንድ በፊትህ እንደ ቆምሁ አስብ። 21 ስለዚህ ልጆቻቸውን ለራብ ስጥ፤ ለሰይፍም እጅ አሳልፈህ ስጣቸው፤ ሚስቶቻቸውም የወላድ መካንና መበለቶች ይሁኑ፤ ወንዶቻቸውም በሞት ይጥፉ፤ ጐልማሶቻቸውም በጦርነት ጊዜ በሰይፍ ይመቱ። 22 ሊይዙኝ ጕድጓድ ቈፍረዋልና፥ ለእግሮችም ወጥመድ ሸሽገዋልና፥ በቤታቸው ጩኸት ይሰማ፤ ድንገትም በላያቸው ወንበዴን አምጣባቸው። 23 አንተ ግን አቤቱ! ይገድሉኝ ዘንድ በላዬ የመከሩትን ምክር ሁሉ ታውቃለህ፤ በደላቸውንም ይቅር አትበል፤ ኀጢአታቸውንም ከፊትህ አትደምስስ፤ በፊትህም ይውደቁ፤ በቍጣህ ጊዜ እንዲሁ አድርግባቸው።” |