ዘፍጥረት 26 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)ይስሐቅ ወደ ጌራራ መሄዱ 1 በምድርም ቀድሞ በአብርሃም ዘመን ከሆነው ራብ ሌላ ራብ ሆነ፤ ይስሐቅም ወደ ፍልስጥኤም ንጉሥ ወደ አቤሜሌክ ወደ ጌራራ ሄደ። 2 እግዚአብሔርም ተገለጠለት፤ እንዲህም አለው፥ “ወደ ግብፅ አትውረድ፤ እኔ በምልህ ምድር ተቀመጥ። 3 በዚህች ምድር ተቀመጥ፤ ከአንተ ጋርም እሆናለሁ፤ እባርክሃለሁም፤ ይህችን ምድር ሁሉ ለአንተም፥ ለዘርህም እሰጣለሁና፥ ለአባትህም ለአብርሃም የማልሁለትን መሐላ ከአንተ ጋር አጸናለሁ። 4 ዘርህንም እንደ ሰማይ ከዋክብት አበዛዋለሁ፤ ይህችንም ምድር ሁሉ ለዘርህ እሰጣለሁ፤ የምድርም ሕዝቦች ሁሉ በዘርህ ይባረካሉ፤ 5 አባትህ አብርሃም ቃሌን ሰምቶአልና፤ ትእዛዜንና ፍርዴን፥ ሥርዐቴንና ሕጌንም ጠብቆአልና።” 6 ይስሐቅም በጌራራ ተቀመጠ። የዚያም ስፍራ ሰዎች ስለ ሚስቱ ስለ ርብቃ ጠየቁት፤ እርሱም፥ “እኅቴ ናት” አላቸው፤ 7 የዚህ ስፍራ ሰዎች ለርብቃ ሲሉ እንዳይገድሉኝ ብሎ ሚስቴ ናት ማለትን ፈርቶአልና፤ እርስዋም ውብ ነበረችና። 8 በዚያም ብዙ ቀን ተቀመጠ። የፍልስጥኤም ንጉሥ አቤሜሌክም በመስኮት ሆኖ በተመለከተ ጊዜ ይስሐቅን ከሚስቱ ከርብቃ ጋር ሲጫወት አየው። 9 አቤሜሌክም ይስሐቅን ጠራ፤ እንዲህም አለው፥ “እነሆ፥ ሚስትህ ናት፤ እንዴትስ እርስዋን፦ ‘እኅቴ ናት’ አልህ?” ይስሐቅም፥ “በእርስዋ ምክንያት እንዳልሞት ብዬ ነው” አለው። 10 አቤሜሌክም አለ፥ “ይህ ያደረግህብን ምንድን ነው? ከሕዝቡ አንዱ ባለማወቅ ከሚስትህ ጋር ሊተኛ ጥቂት በቀረው ነበር፤ ኀጢአትንም ልታመጣብን ነበር።” 11 አቤሜሌክም ሕዝቡን ሁሉ፥ “ይህን ሰው፥ ሚስቱንም የሚነካ ፍርዱ ክፉ ሞት ነው” ብሎ አዘዘ። 12 ይስሐቅም በዚያች ምድር ዘርን ዘራ፤ በዚያች ዓመትም መቶ እጥፍ ገብስ አገኘ፤ እግዚአብሔርም ባረከው። 13 ከፍ ከፍም አለ፤ እጅግም ታላቅ እስኪሆን ድረስ እየጨመረ ይበዛ ነበር፤ 14 ወንዶችና ሴቶች አገልጋዮችን፥ ብዙ በጎችንና ላሞችን፥ የእርሻ መሬትንም ገዛ፤ የፍልስጥኤም ሰዎችም ቀኑበት። 15 በአባቱ በአብርሃም ዘመን የአባቱ ሎሌዎች የማሱአቸውን ጕድጓዶች ሁሉ የፍልስጥኤም ሰዎች ደፈኑአቸው፤ አፈርንም ሞሉባቸው። 16 አቤሜሌክም ይስሐቅን፥ “ከእኛ ተለይተህ ሂድ፤ ከእኛ ይልቅ እጅግ በርትተሃልና” አለው። 17 ይስሐቅም ከዚያ ሄደ፤ በጌራራም ሸለቆ ሰፈረ፤ በዚያም ተቀመጠ። 18 ይስሐቅም የአባቱ የአብርሃም አገልጋዮች ቈፍረዋቸው የነበሩትን የውኃ ጕድጓዶች ደግሞ አስቈፈረ፤ አባቱ አብርሃም ከሞተ በኋላ የፍልስጥኤም ሰዎች ደፍነዋቸው ነበርና፤ አባቱም አብርሃም ይጠራቸው በነበረው ስም ጠራቸው። 19 የይስሐቅ ሎሌዎችም በጌራራ ሸለቆ ውስጥ ጕድጓድ ቈፈሩ፤ በዚያም ጣፋጭ የውኃ ምንጭ አገኙ። 20 የጌራራ እረኞች ከይስሐቅ እረኞች ጋር፥ “ውኃው የእኛ ነው” ሲሉ ተጣሉ፤ የዚያችንም ጕድጓድ ስም “ዐዘቅተ ዐመፃ” ብሎ ጠራት፤ እነርሱ በድለውታልና። 21 ይስሐቅም ከዚያ ሄደ በዚያም ሌላ ጕድጓድ ማሰ፥ ስለ እርስዋም ደግሞ ተጣሉት፤ ስምዋንም “ጽልእ” ብሎ ጠራት። 22 ከዚያም እልፍ ብሎ ሌላ ጕድጓድ ቈፈረ፤ ስለ እርስዋም አልተጣሉትም፤ ስምዋንም “መርኅብ” ብሎ ጠራት፤ እንዲህ ሲል፥ “አሁን እግዚአብሔር አሰፋልን፤ በምድርም አበዛን።” 23 ከዚያም ወደ ዐዘቅተ መሐላ ሄደ። 24 በዚያችም ሌሊት እግዚአብሔር ተገለጠለት፤ እንዲህም አለው፥ “እኔ የአባትህ የአብርሃም አምላክ ነኝ፤ አትፍራ፤ እኔ ከአንተ ጋር ነኝና፤ እባርክሃለሁ፤ ስለ አባትህ ስለ አብርሃም ዘርህን አበዛዋለሁ።” 25 በዚያም ለአምላኩ ለእግዚአብሔር መሠውያን ሠራ፤ የእግዚአብሔርንም ስም ጠራ፤ በዚያም ድንኳን ተከለ፤ የይስሐቅም ሎሌዎች በዚያ ጕድጓድ ማሱ። በይስሐቅና በአቤሜሌክ መካከል የተደረገ ስምምነት 26 አቤሜሌክና ሚዜው አኮዘት፥ የሠራዊቱም አለቃ ፋኮል ከጌራራ ወደ እርሱ ሄዱ። 27 ይስሐቅም፥ “ለምን ወደ እኔ መጣችሁ? እናንተ ጠልታችሁኛል፤ ከእናንተም ለይታችሁ አሳድዳችሁኛልና” አላቸው። 28 እነርሱም አሉት፥ “እኛ የጠላንህ አይደለም፤ በመልካም አኑረን፥ በመልካም አሰናበትንህ እንጂ፥ አሁንም አንተ ለአምላክህ ለእግዚአብሔር ቡሩክ ነህ። 29 አምላክህ እግዚአብሔርም ከአንተ ጋር እንደ አለ በአየን ጊዜ በአንተና በእኛ መካከል መሐላ ይሁን፤ አንተ በእኛ ላይ ክፉ እንዳታደርግ፤ እኛም በአንተ ላይ ክፉ እንዳናደርግ እንማማላለን።” 30 ይስሐቅም ማዕድ አቀረበላቸው፤ በሉም፤ ጠጡም። 31 ማልደውም ተነሡ፤ እርስ በርሳቸውም ተማማሉ፤ ይስሐቅም አሰናበታቸው፤ ከእርሱም በደኅና ሄዱ። 32 በዚያም ቀን የይስሐቅ ሎሌዎች መጡ፤ ስለ ቈፈሩአትም ጕድጓድ፥ ውኃ አገኘን ብለው ነገሩት። 33 ስምዋንም “መሐላ” ብሎ ጠራት፤ ስለዚህም የከተማዪቱ ስም እስከ ዛሬ ድረስ “ዐዘቅተ መሐላ” ይባላል። ዔሳው ከከነዓን ሚስቶችን እንደ አገባ 34 ዔሳውም አርባ ዓመት ሲሆነው የኬጢያዊው የብኤልን ልጅ ዮዲትን፥ የኬጢያዊው የኤሎንን ልጅ ቤሴሞትንም ሚስቶች አድርጎ አገባ፤ 35 እነርሱም ይስሐቅንና ርብቃን ያሳዝኑ ነበር። |