ዘፍጥረት 20 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)አብርሃምና አቤሜሌክ 1 አብርሃምም ከዚያ ተነሥቶ ወደ አዜብ ምድር አቅጣጫ ሄደ፤ በቃዴስና በሱር መካከልም ኖረ፤ በጌራራም በእንግድነት ተቀመጠ። 2 አብርሃምም ሚስቱን ሣራን “እኅቴ ናት” አላቸው፤ የከተማዪቱ ሰዎች ስለ እርስዋ እንዳይገድሉት “ሚስቴ” ናት ማለትን ፈርቶአልና፤ የጌራራ ንጉሥ አቤሜሌክም ላከና ሣራን ወሰዳት። 3 በዚያች ሌሊትም አቤሜሌክ ተኝቶ ሳለ እግዚአብሔር በሕልም ወደ እርሱ መጣ፤ እንዲህም አለው፥ “እነሆ፥ አንተ ስለ ወሰድሃት ሴት ትሞታለህ፤ እርስዋ ባለ ባል ናትና።” 4 አቤሜሌክ ግን አልቀረባትም ነበር፤ አቤሜሌክም እንዲህ አለ፥ “አቤቱ ያላወቀውን ሕዝብ በእውነት ታጠፋለህን? 5 እኅቴ ናት ያለኝ እርሱ አይደለምን? እርስዋ ደግሞ ራስዋ ወንድሜ ነው አለች፤ በልቤ ቅንነትና በእጄ ንጹሕነት ይህን አደረግሁት።” 6 እግዚአብሔርም በሕልም አለው፥ “ይህን በልብህ ቅንነት እንዳደረግህ እኔ ዐወቅሁ፤ እኔም ደግሞ በፊቴ ኀጢአትን እንዳትሠራ ጠበቅሁህ፤ ስለዚህም ትቀርባት ዘንድ አልተውሁህም። 7 አሁንም የሰውየውን ሚስት መልስ፤ ነቢይ ነውና፥ ስለ አንተም ይጸልያል፤ ትድናለህም። ባትመልሳት ግን አንተ እንድትሞት፥ ለአንተ የሆነውም ሁሉ እንዲሞት በርግጥ ዕወቅ።” 8 አቤሜሌክም በጥዋት ተነሣ፤ ብላቴኖቹንም ሁሉ ጠራ፤ ይህንም ነገር ሁሉ በጆሮአቸው ተናገረ፤ ቤተ ሰዎቹም ሁሉ እግዚአብሔርን እጅግ ፈሩ። 9 አቤሜሌክም አብርሃምን ጠርቶ አለው፥ “ይህ ያደረግህብን ምንድን ነው? ምንስ ክፉ ሠራሁብህ? በእኔና በመንግሥቴ ላይ ትልቅ ኀጢአት አውርደሃልና፤ ማንም የማያደርገው የማይገባ ሥራ በእኔ ሠራህብኝ።” 10 አቤሜሌክም አብርሃምን አለው፥ “ይህን ነገር ማድረግህ ምን አይተህ ነው?” 11 አብርሃምም አለ፥ “ምንአልባት በዚህ ስፍራ እግዚአብሔርን መፍራት ስለሌለ በሚስቴ ምክንያት ይገድሉኛል ብዬ ነው። 12 እርስዋም ደግሞ በእናቴ ወገን አይደለችም እንጂ በእውነት በአባቴ ወገን እኅቴ ናት፤ ለእኔም ሚስት ሆነች። 13 እግዚአብሔርም ከአባቴ ቤት ባወጣኝ ጊዜ አልኋት፥ ‘ይህን ጽድቅ አድርጊልኝ፤ በገባንበት ሀገር ሁሉ ወንድሜ ነው በዪ።’ ” 14 አቤሜሌክም አንድ ሺህ ምዝምዝ ብርን በጎችንና ላሞችን፥ ወንዶችና ሴቶች ባሪያዎችን አመጣ፤ ለአብርሃምም ሰጠው፤ ሚስቱን ሣራንም መለሰለት። 15 አቤሜሌክም አብርሃምን አለው፥ “እነሆ፥ ምድሬ በፊትህ ናት፤ በወደድኸው ተቀመጥ።” 16 ሣራንም አላት “እነሆ፥ ለወንድምሽ አንድ ሺህ ምዝምዝ ብር ሰጠሁት፤ ይህም ለፊትሽ ክብር ይሁንሽ፤ በሁሉም እውነትን ተናገራት።” 17 አብርሃምም ወደ እግዚዘብሔር ጸለየ፤ እግዚአብሔርም አቤሜሌክን፥ ሚስቱንም፥ ሴቶች ልጆቹንም፥ በቤቱ ውስጥ ያሉ ሴቶች አገልጋዮቹንም ፈወሳቸው፤ እነርሱም ወለዱ፤ 18 እግዚአብሔር በአብርሃም ሚስት በሣራ ምክንያት በአቤሜሌክ ቤት ማኅፀኖችን ሁሉ በፍጹም ዘግቶ ነበርና። |