ዘፍጥረት 16 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)አጋርና ይስማኤል 1 የአብራም ሚስት ሦራ ግን ልጅ አልወለደችለትም ነበር፤ ስምዋ አጋር የተባለ ግብፃዊት አገልጋይም ነበረቻት። 2 ሦራም አብራምን፥ “እነሆ፥ እንዳልወልድ እግዚአብሔር ዘጋኝ፤ ከእርስዋ ትወልድ ዘንድ ወደ አገልጋዬ ሂድ” አለችው። አብራምም የሚስቱን የሦራን ቃል ሰማ። 3 አብራምም በከነዓን ምድር ዐሥር ዓመት ከተቀመጠ በኋላ፥ የአብራም ሚስት ሦራ ግብፃዊት አገልጋይዋን አጋርን ወስዳ ለአብራም ሚስት ትሆነው ዘንድ ሰጠችው። 4 አብራምም ወደ አጋር ገባ፤ ፀነሰችም፤ እንደ ፀነሰችም ባየች ጊዜ እመቤቷን ማክበርዋን ተወች። 5 ሦራም አብራምን፥ “ከአንተ የተነሣ እገፋለሁ፤ እኔ አገልጋዬን በብብትህ ሰጠሁህ፤ እንደ ፀነሰችም ባየች ጊዜ እኔን ማክበርን ተወች፤ እግዚአብሔር በእኔና በአንተ መካከል ይፍረድ” አለችው። 6 አብራምም ሚስቱን ሦራን፥ “እነሆ፥ አገልጋይሽ በእጅሽ ናት፤ እንደ ወደድሽ አድርጊባት” አላት። ሦራም አጋርን አሠቃየቻት፤ ከእርስዋም ኰበለለች። 7 የእግዚአብሔር መልአክም በውኃ ምንጭ አጠገብ በሱር በረሃ በመንገድ አገኛት። 8 የእግዚአብሔርም መልአክ፥ “የሦራ አገልጋይ አጋር ሆይ፥ ከወዴት መጣሽ? ወዴትስ ትሄጂያለሽ?” አላት። እርስዋም፥ “እኔ ከእመቤቴ ከሦራ ፊት እኰበልላለሁ” አለች። 9 የእግዚአብሔር መልአክም፥ “ወደ እመቤትሽ ተመለሺ፤ ከእጅዋም በታች ራስሽን ዝቅ አድርጊ” አላት። 10 እግዚአብሔርም “ከብዛቱ የተነሣ እስከማይቈጠር ድረስ ዘርሽን እጅግ አበዛለሁ፥” አላት። 11 የእግዚአብሔር መልአክም አላት፥ “እነሆ፥ አንቺ ፀንሰሻል፤ ወንድ ልጅንም ትወልጃለሽ፤ ስሙንም ይስማኤል ብለሽ ትጠሪዋለሽ፤ እግዚአብሔር ሥቃይሽን ሰምቶአልና። 12 እርሱም የበረሃ ሰው ይሆናል፤ እጁ በሁሉ ላይ ይሆናል፤ የሁሉም እጅ ደግሞ በእርሱ ላይ ይሆናል፤ እርሱም በወንድሞቹ ሁሉ ፊት ይኖራል።” 13 አጋርም ይናገራት የነበረውን የእግዚአብሔርን ስም ጠራች፤ “አቤቱ የራራህልኝ አንተ ነህ፤ የተገለጠልኝን በፊቴ አይችዋለሁና።” 14 ስለዚህም የዚያን ጕድጓድ ስም “በፊቴ የተገለጠልኝ የእርሱ ጕድጓድ” ብላ ጠራችው፤ እርሱም በቃዴስና በባሬድ መካከል ነው። አጋርም ተመለሰች። 15 ከዚህም በኋላ አጋር ለአብራም ወንድ ልጅን ወለደችለት፤ አብራምም አጋር የወለደችለትን የሕፃኑን ስም ይስማኤል ብሎ ጠራው። 16 አጋር ይስማኤልን በወለደችለት ጊዜ አብራም የሰማንያ አምስት ዓመት ሰው ነበረ። |