ዘፍጥረት 11 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)የሰናዖር ግንብ 1 የዓለም ሁሉ ቋንቋ አንድ፥ ንግግሩም አንድ ነበረ። 2 እንዲህም ሆነ፤ ከምሥራቅም ተነሥተው በሄዱ ጊዜ በሰናዖር ምድር አንድ ሜዳ አገኙ፤ በዚያም ተቀመጡ። 3 እርስ በርሳቸውም፥ “ኑ ጡብ እንሥራ፤ በእሳትም እንተኵሰው” ተባባሉ። ጡባቸውም እንደ ድንጋይ፥ ጭቃቸውም እንደ ዝፍት ሆነላቸው። 4 እርስ በርሳቸውም፥ “ኑ ለእኛ ከተማና ራሱ ወደ ሰማይ የሚደርስ ግንብ እንሥራ፤ በምድር ፊት ሁሉ ላይ ሳንበተን ስማችንን እናስጠራው” ተባባሉ። 5 እግዚአብሔርም የሰዎች ልጆች የሠሩትን ከተማና ግንብ ለማየት ወረደ። 6 እግዚአብሔርም አለ፥ “እነሆ፥ እነርሱ አንድ ወገን ናቸው፤ ለሁሉም አንድ ቋንቋ አላቸው፤ ይህንም ለማድረግ ጀመሩ፤ አሁንም ያሰቡትን ሁሉ መሥራትን አይተዉም። 7 ኑ እንውረድ፤ አንዱ የሌላውን ነገር እንዳይሰማው ቋንቋቸውን በዚያ እንደባልቀው።” 8 እግዚአብሔርም ቋንቋቸውን ለያየ፤ ከዚያም በምድር ፊት ሁሉ ላይ በተናቸው፤ ከዚያም በኋላ ከተማዪቱንና ግንቡን መሥራትን ተዉ። 9 ስለዚህም ስምዋ ባቢሎን ተባለ፤ እግዚአብሔር በዚያ የምድርን ቋንቋ ሁሉ ደባልቆአልና፤ ከዚያም እግዚአብሔር በምድር ሁሉ ፊት ላይ እነርሱን በትኖአቸዋል። የሴም ትውልድ ( 1ዜ.መ. 1፥24-27 ) 10 የሴም ትውልድ ይህ ነው። ሴም ከጥፋት ውኃ በኋላ በሁለተኛው ዓመት አርፋክስድን በወለደ ጊዜ የመቶ ዓመት ሰው ነበረ። 11 ሴምም አርፋክስድን ከወለደ በኋላ አምስት መቶ ዓመት ኖረ፤ ወንዶችንም፥ ሴቶችንም ወለደ፤ ሞተም። 12 አርፋክስድም መቶ ሠላሳ አምስት ዓመት ኖረ፤ ቃይናንንም ወለደ፤ 13 አርፋክስድም ቃይናንን ከወለደ በኋላ አራት መቶ አርባ ዓመት ኖረ፤ ወንዶችንም፥ ሴቶችንም ወለደ፤ ሞተም። ቃይናንም መቶ ሠላሳ ዓመት ኖረ፤ ሳላንም ወለደ፤ ቃይናንም ሳላን ከወለደ በኋላ አራት መቶ ሠላሳ ዓመት ኖረ፤ ወንዶችንም፥ ሴቶችንም ልጆች ወለደ፤ ሞተም። 14 ሳላም መቶ ሠላሳ ዓመት ኖረ፤ ዔቦርንም ወለደ፤ 15 ሳላም ዔቦርን ከወለደ በኋላ አራት መቶ ሠላሳ ዓመት ኖረ፤ ወንዶችንም ሴቶችንም ወለደ፤ ሞተም። 16 ዔቦርም መቶ ሠላሳ አራት ዓመት ኖረ፤ ፋሌቅንም ወለደ፤ 17 ዔቦርም ፋሌቅን ከወለደ በኋላ አራት መቶ ሠላሳ ዓመት ኖረ፤ ወንዶችንም፥ ሴቶችንም ወለደ፤ ሞተም። 18 ፋሌቅም መቶ ሠላሳ ዓመት ኖረ፤ ራግውንም ወለደ፤ 19 ፋሌቅም ራግውን ከወለደ በኋላ ሁለት መቶ ዘጠኝ ዓመት ኖረ፤ ወንዶችንም፥ ሴቶችንም ወለደ፤ ሞተም። 20 ራግውም መቶ ሠላሳ ሁለት ዓመት ኖረ፤ ሴሮሕንም ወለደ፤ 21 ራግውም ሴሮሕን ከወለደ በኋላ ሁለት መቶ ሰባት ዓመት ኖረ፤ ወንዶችንም ሴቶችንም ወለደ፤ ሞተም። 22 ሴሮሕም መቶ ሠላሳ ዓመት ኖረ፤ ናኮርንም ወለደ፤ 23 ሴሮሕም ናኮርን ከወለደ በኋላ ሁለት መቶ ዓመት ኖረ፤ ወንዶችንም፥ ሴቶችንም ወለደ፤ ሞተም። 24 ናኮርም መቶ ዘጠኝ ዓመት ኖረ፤ ታራንም ወለደ፤ 25 ታራንም ከወለደ በኋላ ናኮር መቶ ሀያ ዘጠኝ ዓመት ኖረ፤ ወንዶችንም፥ ሴቶችንም ወለደ፤ ሞተም። የታራ ትውልድ 26 ታራም መቶ ዓመት ኖረ፥ አብራምንና ናኮርን፥ አራንንም ወለደ። 27 አራንም ሎጥን ወለደ። 28 አራንም በተወለደባት ሀገር በከለዳውያን ምድር በአባቱ በታራ ፊት ሞተ። 29 አብራምና ናኮርም ሚስቶችን አገቡ፤ የአብራም ሚስት ስምዋ ሦራ ነው፤ የናኮርም ሚስት የአራን ልጅ ሚልካ ናት፤ አራንም የሚልካና የዮስካ አባት ነው። 30 ሦራም መካን ነበረች፤ ልጆችም አልነበሩአትም። 31 ታራም ልጁን አብራምንና የልጅ ልጁን የአራንን ልጅ ሎጥን፥ የልጁንም የአብራምን ሚስት ምራቱን ሦራን ወሰደ፤ ከእርሱም ጋር ወደ ከነዓን ምድር ይሄዱ ዘንድ ከከለዳውያን ምድር አወጣቸው። ወደ ካራንም መጡ፤ በዚያም ተቀመጡ። 32 ታራም በካራን ምድር የኖረበት ዘመን ሁለት መቶ አምስት ዓመት ሆነ፤ ታራም በካራን ሞተ። |