ዘዳግም 8 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)የተስፋይቱን ምድር ለመውረስ የተሰጠ መመሪያ 1 “በሕይወት እንድትኖሩ፥ እንድትበዙም፥ እግዚአብሔርም ለአባቶቻችሁ ወደ ማለላቸው ምድር ገብታችሁ እንድትወርሱአት፥ ዛሬ ለአንተ የማዝዘውን ትእዛዝ ሁሉ ታደርጉ ዘንድ ጠብቁ። 2 አምላክህ እግዚአብሔር ይፈትንህ ዘንድ፥ በልብህም ያለውን ትእዛዙን ትጠብቅ ወይም አትጠብቅ እንደ ሆነ ያውቅ ዘንድ፥ ሊያስጨንቅህ በምድረ በዳ የመራህን መንገድ ሁሉ አስብ። 3 ሰውም ከእግዚአብሔር አፍ በሚወጣ ነገር ሁሉ በሕይወት እንዲኖር እንጂ ሰው በእንጀራ ብቻ በሕይወት እንዳይኖር ያስታውቅህ ዘንድ አስጨነቀህ፥ አስራበህም፤ አንተም ያላወቅኸውን፥ አባቶችህም ያላወቁትን መና መገበህ። 4 የለበስኸው ልብስ አላረጀም፤ እግርህም አልነቃም፤ እነሆ፥ አርባ ዓመት ሆነ። 5 ሰውም ልጁን እንደሚገሥጽ እንዲሁ አምላክህ እግዚአብሔር አንተን እንዲገሥጽ በልብህ ዕወቅ። 6 በመንገዱም እንድትሄድ፥ እርሱንም እንድትፈራ የአምላክህን የእግዚአብሔርን ትእዛዝ ጠብቅ። 7 አምላክህ እግዚአብሔር ወደ መልካምና ሰፊ ምድር፥ ከሜዳና ከተራሮች የሚመነጩ የውኃ ጅረቶችና ፈሳሾችም ወዳሉባት ምድር፥ 8 ስንዴ፥ ገብስም፥ ወይንም፥ በለስም፥ ሮማንም ወደ ሞሉባት፥ ወይራም፥ ቅቤም፥ ማርም ወደ ሞሉባት ምድር፥ 9 ሳይጐድልህ እንጀራን ወደምትበላባት፥ አንዳችም ወደማታጣባት ምድር፥ ድንጋይዋ ብረት ወደ ሆነ፥ ከተራራዋም መዳብ ወደሚማስባት ምድር ያገባሃል። 10 ትበላማለህ፤ ትጠግብማለህ፤ ስለ ሰጠህም ስለ መልካሚቱ ምድር አምላክህን እግዚአብሔርን ታመሰግናለህ። እግዚአብሔርን እንዳይረሱ የተሰጠ ማስጠንቀቂያ 11 “ዛሬ እኔ አንተን የማዝዘውን ትእዛዙንና ፍርዱን፥ ሥርዐቱንም ባለመጠበቅ አምላክህን እግዚአብሔርን እንዳትረሳ ተጠንቀቅ፤ 12 ከበላህና ከጠገብህ በኋላ፥ መልካምም ቤት ሠርተህ ከተቀመጥህባት በኋላ፤ 13 የላምና የበግ መንጋ ከበዛልህ በኋላ፥ ብርህና ወርቅህም፥ ያለህም ሁሉ ከበዛልህ በኋላ፥ ልብህ እንዳይታበይ፤ 14 ከግብፅ ምድር ከባርነት ቤት ያወጣህን፥ 15 የሚናደፍ እባብና ጊንጥ፥ ጥማትም ባለባት፥ ውኃም በሌለባት፥ በታላቂቱና በምታስፈራው ምድረ በዳ የመራህን፥ ከጭንጫ ድንጋይም ጣፋጭ ውኃን ያወጣልህን፥ 16 በመጨረሻም ዘመን መልካም ያደርግልህ ዘንድ ሊፈትንህ፥ ሊያዋርድህም አባቶችህ ያላወቁትን መና በምድረ በዳ የመገበህን አምላክህን እግዚአብሔርን እንዳትረሳ፥ 17 በልብህም፦ በጕልበቴ፥ በእጄም ብርታት ይህን ሁሉ ታላቅ ኀይል አደረግሁ እንዳትል። 18 ነገር ግን ዛሬ እንደ ሆነ ለአባቶችህ የማለውን ቃል ኪዳን ያጸና ዘንድ እርሱ ኀይልን ስለሚሰጥህ አምላክህን እግዚአብሔርን አስበው። 19 አምላክህንም እግዚአብሔርን ፈጽሞ ብትረሳ፥ ሌሎችንም አማልክት ብትከተል፥ ብታመልካቸውም፥ ብትሰግድላቸውም፥ ፈጽሞ እንደምትጠፋ እኔ ዛሬውኑ ሰማይንና ምድርን አስመሰክርብሃለሁ። 20 የአምላካችሁን የእግዚአብሔርን ቃል ስለ አልሰማችሁ እግዚአብሔር ከፊታችሁ እንደሚአጠፋቸው እንደ አሕዛብ ሁሉ እናንተም እንዲሁ ትጠፋላችሁ። |