ዘዳግም 34 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)የሙሴ መሞትና መቀበር 1 ሙሴም ከሞዓብ ሜዳ በኢያሪኮ ፊት ለፊት ወዳለው ወደ ናባው ተራራ ወደ ፈስጋ ራስ ወጣ፤ እግዚአብሔርም እስከ ዳን ድረስ ያለውን የገለዓድን ምድር አሳየው፤ 2 የንፍታሌምንም ምድር ሁሉ፥ የምናሴንም ምድር ሁሉ፥ እስከ ምዕራብም ባሕር ድረስ ያለውን የይሁዳን ምድር ሁሉ፤ 3 ምድረ በዳውን፥ የኢያሪኮን ዙሪያ፥ እስከ ሴይር ዙሪያ ያለውንም የፊንቆንን ከተማ አሳየው፤ 4 እግዚአብሔርም ሙሴን፥ “ለዘርህ እሰጣታለሁ ብዬ ለአብርሃምና ለይስሐቅ ለያዕቆብም የማልሁላቸው ምድር ይህች ናት፤ እነሆም፥ በዐይንህ እንድታያት አደረግሁህ፤ ነገር ግን ወደዚያች አትገባም” አለው። 5 የእግዚአብሔር አገልጋይ ሙሴም እንደ እግዚአብሔር ቃል በዚያ በሞዓብ ምድር ሞተ። 6 በቤተ ፌጎርም አቅራቢያ በናባው ምድር ቀበሩት፤ እስከ ዛሬም ድረስ መቃብሩን ማንም የሚያውቅ የለም። 7 ሙሴም በሞተ ጊዜ ዕድሜዉ መቶ ሃያ ዓመት ነበረ፤ ዐይኖቹም አልፈዘዙም፤ ጕልበቱም አልደከመም ነበር። 8 የእስራኤልም ልጆች በዮርዳኖስ በኢያሪኮ አቅራቢያ በሞዓብ ሜዳ ሠላሳ ቀን ለሙሴ አለቀሱለት፤ ለሙሴም ያለቀሱለት የልቅሶው ወራት ተፈጸመ። 9 ሙሴም እጆቹን ስለ ጫነበት የነዌ ልጅ ኢያሱ የጥበብን መንፈስ ተሞላ፤ የእስራኤልም ልጆች ታዘዙለት፤ እግዚአብሔርም ሙሴን እንዳዘዘው አደረጉ። 10 እግዚአብሔር ፊት ለፊት እንደ ተናገረው እንደ ሙሴ ያለ ነቢይ ከዚያ ወዲህ በእስራኤል ዘንድ አልተነሣም፤ 11 በግብፅ ምድር በፈርዖንና በሹሞቹ ሁሉ ላይ፥ በምድሪቱም ሁሉ ላይ ምልክትንና ድንቅን ያደርግ ዘንድ እግዚአብሔር እንደ ላከው ያለ፥ 12 በእስራኤል ሁሉ ፊት በታላቅ ተአምር ሁሉና በጸናች እጅ፥ በተዘረጋችም ክንድ ሁሉ እንዳደረገው እንደ ሙሴ ያለ ነቢይ አልተነሣም። |