ዘዳግም 1 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)እስራኤላውያን ሲናን ለቅቀው እንዲጓዙ የተሰጠ ትእዛዝ 1 በዮርዳኖስ ማዶ በምድረ በዳ፥ በምዕራብ በኩል በኤርትራ ባሕር አጠገብ በፋራንና በጦፌል፥ በላባንና በአውሎን፥ በካታኪሪሲያም መካከል፥ ሙሴ ለእስራኤል ሁሉ፥ የነገራቸው ቃላት እኒህ ናቸው። 2 በሴይር ተራራ መንገድ ከኮሬብ እስከ ቃዴስ በርኔ ድረስ የዐሥራ አንድ ቀን ጕዞ ነው። 3 በአርባኛው ዓመት በዐሥራ አንደኛው ወር ከወሩም በመጀመሪያው ቀን፥ ሙሴ እንዲነግራቸው እግዚአብሔር ስለ እነርሱ ያዘዘውን ሁሉ ለእስራኤል ልጆች ነገራቸው፤ 4 በሐሴቦን ተቀምጦ የነበረውን የአሞሬዎናውያንን ንጉሥ ሴዎንን፥ በአስጣሮትና በኤድራይን ተቀምጦ የነበረውንም የባሳንን ንጉሥ ዐግን ከገደሉት በኋላ፥ 5 በዮርዳኖስ ማዶ በሞዓብ ምድር ሙሴ እንዲህ ብሎ ይህን ሕግ ይገልጥ ጀመር፦ 6 “አምላካችን እግዚአብሔር በኮሬብ እንዲህ ብሎ ተናገረን፦ በዚህ ተራራ መቀመጣችሁ በቃ፤ 7 ተመልሳችሁ ተጓዙ፤ ወደ አሞራውያን ተራራ፥ ወደ አረባም ሀገሮች ሁሉ፥ በተራራውም፥ በሜዳውም፥ በሊባም፥ በባሕርም ዳር ወዳሉ ወደ ከነዓናውያን ምድር፥ ወደ ሊባኖስም ፊት ለፊት እስከ ታላቁ ወንዝ እስከ ኤፍራጥስ ድረስ ሂዱ። 8 እነሆ፥ ምድሪቱን ሰጠኋችሁ፤ ግቡ፥ እግዚአብሔር ለእነርሱ፥ ከእነርሱም በኋላ ለዘራቸው ይሰጣት ዘንድ ለአባቶቻችሁ ለአብርሃምና ለይስሐቅ ለያዕቆብም የማለላቸውን ምድር ውረሱ። ሙሴ የሕዝብ አለቆችን መሾሙ ( ዘፀ. 18፥13-27 ) 9 “በዚያም ዘመን እንዲህ ብዬ ተናገርኋችሁ፦ እኔ ብቻዬን ልሸከማችሁ አልችልም፤ 10 አምላካችሁ እግዚአብሔር አብዝቶአችኋልና፥ እነሆም፥ እናንተ ዛሬ እንደ ሰማይ ከዋክብት ብዙዎች ናችሁ። 11 የአባቶቻችሁ አምላክ እግዚአብሔር በዚህ ቍጥር ላይ እልፍ አእላፋት ይጨምር፤ እንደ ተናገራችሁም ይባርካችሁ። 12 እኔ ብቻዬን ድካማችሁን፥ ሸክማችሁንም፥ ክርክራችሁንም እሸከም ዘንድ እንዴት እችላለሁ? 13 ከእናንተ ከየነገዳችሁ ጥበበኞች፥ አስተዋዮችም፥ ዐዋቂዎችም የሆኑትን ሰዎች አምጡ፤ እኔም በላያችሁ አለቆች አደርጋቸዋለሁ። 14 እናንተም፦ ‘እናደርገው ዘንድ የተናገርኸው ይህ ነገር መልካም ነው’ ብላችሁ መልሳችሁ ነገራችሁኝ። 15 ከእናንተም ጥበበኞችና ዐዋቂዎች፥ አስተዋዮችም የሆኑትን ሰዎች ወሰድሁ፤ በእናንተም ላይ አለቆች፥ የሻለቆችም፥ የመቶ አለቆችም፥ የአምሳ አለቆችም፥ የዐሥር አለቆችም፥ ለፈራጆቻችሁም ጻፎች አድርጌ ሰየምኋቸው። 16 በዚያን ጊዜ ፈራጆቻችሁን አዘዝኋቸው። አልኋቸውም፦ የወንድሞቻችሁን ነገር ስሙ፤ በሰውና በወንድሙ፥ ከእርሱም ጋር ባለው መጻተኛ መካከል በጽድቅ ፍረዱ። 17 በፍርድም ፊት አትዩ፤ ለትልቁም፥ ለትንሹም በእውነት ፍረዱ፤ ለሰው ፊት አታድሉ፤ ፍርድ የእግዚአብሔር ነውና። አንድ ነገር ቢከብዳችሁ እርሱን ወደ እኔ አምጡት፤ እኔም እሰማዋለሁ፤ 18 በዚያን ጊዜም ልታደርጉት የሚገባችሁን ነገር ሁሉ አዘዝኋችሁ። ከቃዴስ በርኔ ወደ ከነዓን የተላኩ ጕበኞች ( ዘኍ. 13፥1-33 ) 19 “ከኮሬብም ተጓዝን፤ አምላካችን እግዚአብሔርም እንዳዘዘን በታላቁ፥ እጅግም በሚያስፈራ በዚያ ባያችሁት ምድረ በዳ ሁሉ በኩል በአሞሬዎን ተራራ መንገድ ሄድን፤ ወደ ቃዴስ በርኔም መጣን። 20 እኔም አልኋችሁ፦ አምላካችን እግዚአብሔር እስከ ሰጣችሁ እስከ አሞሬዎን ተራራ ኑ፤ 21 እነሆ፥ አምላካችሁ እግዚአብሔር ምድሪቱን በፊታችሁ እንደ ሰጣችሁ እዩ፤ የአባቶቻችሁ አምላክ እግዚአብሔር እንዳላችሁ ውጡ፤ ውረሷት፤ አትፍሩ፤ አትደንግጡም። 22 እናንተም ሁላችሁ ወደ እኔ ቀርባችሁ፦ ምድሪቱን እንዲሰልሉልንና እንወጣባት ዘንድ የሚገባንን የመንገዱንና የምንገባባቸውን የእነዚያን ከተሞች ወሬ ተመልሰው እንዲነግሩን በፊታችን ሰዎች እንላክ አላችሁኝ። 23 ያም ነገር ደስ አሰኘኝ፤ ከእናንተም ዐሥራ ሁለት ሰው ወሰድሁ፤ ከየነገዱ ሁሉ አንድ አንድ ሰው ነበረ። 24 ሄዱም፤ ወደ ተራራውም ወጡ፤ ወደ ወይን ዘለላ ሸለቆ መጥተው ሰለሉአት። 25 ከምድሪቱም ፍሬ በእጃቸው ወሰዱ፤ ወደ እኛም ይዘውት መጡ፦ ‘አምላካችን እግዚአብሔር የሚሰጠን ምድር መልካም ናት አሉን፤’ 26 “ወደ እርስዋ መውጣትንም እንቢ አላችሁ፤ በአምላካችሁ በእግዚአብሔር ትእዛዝ ላይም ዐመፃችሁ፤ 27 በድንኳናችሁም ውስጥ እንዲህ እያላችሁ አጕረመረማችሁ፦ ‘እግዚአብሔር ስለ ጠላን እንዲያጠፋን በአሞሬዎናውያን እጅ አሳልፎ ይሰጠን ዘንድ ከግብፅ ምድር አወጣን። 28 ወዴት እንወጣለን? ሕዝቡ ታላቅና ብዙ ነው፤ ከእኛም ይጠነክራሉ፤ ከተሞቹም ታላላቆች፥ የተመሸጉም፥ እስከ ሰማይም የደረሱ ናቸው፤ የረዐይትንም ልጆች ደግሞ በዚያ አየናቸው ብለው ወንድሞቻችን ልባችንን አስፈሩት።’ 29 እኔም አልኋችሁ፦ አትደንግጡ፤ ከእነርሱም አትፍሩ፤ 30 በፊታችሁ የሚሄደው አምላካችሁ እግዚአብሔር፥ በግብፅ ምድር እንዳደረገላችሁ ሁሉ፥ ስለ እናንተ አብሮአችሁ ይዋጋል፤ 31 ወደዚህም ስፍራ እስክትመጡ ድረስ በሄዳችሁበት መንገድ ሁሉ፥ ሰው ልጁን እንዲመግብ አምላካችሁ እግዚአብሔር በምድረ በዳ እንደመገባችሁ እናንተ አይታችኋል። 32 ዳሩ ግን በዚህ ነገር አምላካችሁ እግዚአብሔርን አላመናችሁትም። 33 እርሱም ስፍራን እንዲመርጥላችሁ፥ ትሄዱበትም ዘንድ የሚገባውን መንገድ እንዲያሳያችሁ ሌሊት በእሳት፥ ቀን በደመና በፊታችሁ በመንገድ ሲሄድ የነበረውን አላመናችሁትም። እግዚአብሔር እስራኤልን እንደ ቀጣ ( ዘኍ. 14፥20-45 ) 34 “እግዚአብሔርም የቃላችሁን ድምፅ ሰምቶ ተቈጣ፤ እንዲህም ብሎ ማለ፦ 35 ለአባቶቻችሁ እሰጣት ዘንድ የማልሁላቸውን መልካሚቱን ምድር ከእነዚህ ሰዎች ማንም አያይም፥ 36 ከዮፎኒ ልጅ ከካሌብ በስተቀር፥ እርሱ ግን ያያታል፤ እግዚአብሔርን ፈጽሞ ተከትሎአልና የረገጣትን ምድር ለእርሱ፥ ለልጆቹም እሰጣለሁ። 37 እግዚአብሔርም በእናንተ ምክንያት በእኔ ተቈጣ፤ እንዲህም አለ፦ አንተ ደግሞ ወደዚያ አትገባም፤ 38 በፊትህ የሚቆም የነዌ ልጅ ኢያሱ እርሱ ወደዚያ ይገባል፤ እርሱን አበርታው፤ ለእስራኤል ምድሪቱን ያወርሳልና። 39 ደግሞ፦ ይማረካሉ ያላችኋቸው ልጆቻችሁ፥ ዛሬም መልካሙን ከክፉ መለየት የማይችሉ ሕፃኖቻችሁ እነርሱ ወደዚያ ይገባሉ፤ ምድሪቱንም ለእነርሱ እሰጣለሁ፤ ይወርሱአታልም። 40 እናንተ ግን ተመልሳችሁ በኤርትራ ባሕር መንገድ ወደ ምድረ በዳ ሂዱ። 41 “እናንተም፦ እግዚአብሔርን በድለናል፤ አምላካችን እግዚአብሔር እንዳዘዘን ሁሉ እንወጣለን፤ እንዋጋማለን ብላችሁ መለሳችሁልኝ። ከእናንተም ሰው ሁሉ የጦር መሣሪያውን ያዘ፤ ወደ ተራራም ወጣችሁ። 42 እግዚአብሔርም፦ እኔ ከእናንተ ጋር አይደለሁምና በጠላቶቻችሁ ፊት እንዳትወድቁ አትውጡ፤ አትዋጉም በላቸው አለኝ። 43 እኔም ተናገርኋችሁ፤ እናንተ ግን አልሰማችሁም፤ የእግዚአብሔርንም ቃል ተላለፋችሁ፤ በኀይላችሁም ወደ ተራራማው አገር ወጣችሁ። 44 በዚያም ተራራማ አገር ይኖሩ የነበሩ አሞሬዎናውያን ወጥተው ተጋጠሙአችሁ፤ ንብ እንደምትነድፍም ነደፉአችሁ፤ አሳደዱአችሁም፤ ከሴይር እስከ ሔርማም ድረስ መቱአችሁ። 45 ተቀምጣችሁም በአምላካችን በእግዚአብሔር ፊት አለቀሳችሁ፤ እግዚአብሔር ግን ድምፃችሁን አልሰማም፤ ወደ እናንተም አልተመለከተም። 46 ቀድሞ እንደ ተቀመጣችሁበትም ዘመን መጠን በቃዴስ ብዙ ቀን ተቀመጣችሁ። |