2 ቆሮንቶስ 9 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)ስለ ቅዱሳን አገልግሎት 1 ለቅዱሳን ስለሚደረገው አገልግሎት የምጽፍላችሁ ብዙ አለኝ 2 እናንተ እንደምትተጉ አውቃለሁና፤ ስለዚህም “የአካይያ ሰዎች እኮ ከአምና ጀምሮ አዘጋጅተዋል” ብዬ በመቄዶንያ ሰዎች ዘንድ አመሰገንኋችሁ፤ እነሆም የእናንተ መፎካከር ብዙዎችን ሰዎች አትግቶአቸዋል። 3 በዚህም ያመሰገንናችሁ ምስጋና በእነርሱ ዘንድ ሐሰት እንዳይሆንብን፥ እንደ ነገርናቸውም ተዘጋጅታችሁ እንዲያገኙአችሁ ወንድሞችን ወደ እናንተ ላክናቸው። 4 ምናልባት የመቄዶንያ ሰዎች ከእኔ ጋር ቢመጡና ሳታዘጋጁ ቢያገኙአችሁ እናንተ ታፍራላችሁ ባልልም እኛ ስለ እናንተ ከነገርናቸው የተነሣ እናፍራለን። 5 ስለዚህም አስቀድመው ወደ እናንተ መጥተው በቅድሚያ የተናገራችኋትን በረከታችሁን እንዲያዘጋጁ ወንድሞችን ማለድሁ፤ እንደዚህም የተዘጋጀ ይሁን፤ በረከትን እንደምታገኙበት እንጂ በንጥቂያ እንደ ተወሰደባችሁ አይሁን። 6 አሳንሶ የሚዘራ ለእርሱ እንዲሁ መከሩ ያንስበታል፤ በብዙ የሚዘራ ግን በብዙ ያመርታል። 7 ሁሉ ልቡ እንደ ወደደ ያድርግ፤ በደስታ ይስጡ እንጂ በግድ አይሆንም፤ እግዚአብሔር በደስታ የሚሰጠውን ይወዳልና። 8 እግዚአብሔር መልካሙን ነገር ሁሉ ሊያበዛላችሁ ይችላል፤ ፍጹም በረከቱንም ለዘወትር ያበዛላችሁ ዘንድ፥ ለሁሉም ታተርፉታላችሁ፤ በጎ ሥራ መሥራትንም ታበዛላችሁ። 9 “በተነ፤ ለድሃም ሰጠ፤ ጽድቁም ለዘለዓለም ይኖራል” ብሎ መጽሐፍ እንደ ተናገረ። 10 እርሱ ዘርን ለዘሪ ይሰጣል፤ እህልንም ለምግብ ይሰጣችኋል፤ ዘራችሁንም ያበዛላችኋል፤ የጽድቃችሁንም መከር ያበጃል። 11 ለብዙ ሰዎች ስለ ሰጣችሁም የእግዚአብሔርን ምስጋና በምታደርግላችሁ ልግስና ሁሉ ባለጸጎች ትሆናላችሁ። 12 ይህቺ የዚህ ሥራ አገልግሎት ግዳጅ የምትፈጽመው ለዚህ ለቅዱሳን ችግር መሟላት ብቻ አይደለም፤ በቅዱሳን ዘንድም ደግሞ የእግዚአብሔርን ምስጋና ታበዛለች። 13 ክርስቶስ ላስተማራት ትምህርት ታዝዛችኋልና፥ ሁላችሁም ደስ ብሎአችሁና ተባብራችሁ አወጣጥታችኋልና በዚች በሃይማኖታችሁ ፈተና ምክንያት እግዚአብሔርን ያመሰግኑታል፤ 14 እነርሱም ስለ እናንተ ይጸልያሉ፤ ስለ አደረባችሁ ታላቅ የእግዚአብሔር ጸጋም ሊያዩአችሁ ይመኛሉ። 15 ስለማትመረመርና ባላሰቡአት ጊዜ ስለምትመጣው ጸጋው እግዚአብሔር ይመስገን። |