2 ቆሮንቶስ 3 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)ስለ ደቀ መዛሙርት 1 ወንድሞቻችን አሁን ደግሞ ራሳችንን እያመሰገን ልንነግራችሁ እንጀምራለንን? ወይስ እንደ ሌሎች ስለ እኛ ወደ እናንተ ደብዳቤ እንዲጽፉላችሁ፥ ወይስ እናንተ ትጽፉልን ዘንድ የምንሻው አለን? 2 የእኛስ መጽሐፋችን እናንተ ናችሁ፤ በልባችን ውስጥም ተጽፋችኋል፤ ትታወቃላችሁም፤ ሰውም ሁሉ ያነብባችኋል። 3 እናንተ ራሳችሁም በእኛ የተላከች የክርስቶስ መልእክት እንደ ሆናችሁ ያውቃሉ፤ ይህቺውም የተጻፈች በሕያው እግዚአብሔር መንፈስ ነው እንጂ በቀለም አይደለም፤ በሥጋ ልብ ሠሌዳነት ነው እንጂ በድንጋይ ሠሌዳም አይደለም። 4 ነገር ግን በክርስቶስ በኩል በእግዚአብሔር ዘንድ እንዲህ ያለ እምነት አለን። 5 ኀይላችን ከእግዚአብሔር ስለ ሆነ ከእኛ ከራሳችን እንደ ሆነ አድርገን ምንም ልናስብ አይገባንም። 6 በመንፈስ እንጂ በፊደል ለማይሆን ለአዲስ ሕግ አገልጋዮች አደረገን፤ ፊደል ይገድላል፥ መንፈስ ግን ሕያው ያደርጋል። ስለ መልእክታት መበላለጥ 7 ስለዚያ ስለ አለፈው የፊቱ ብርሃን የእስራኤል ልጆች የሙሴን ፊት መመልከት እስኪሳናቸው ድረስ በዚያች በድንጋይ ላይ በፊደል ለተቀረጸች ለሞት መልእክት ክብር ከተደረገላት፥ 8 ለመንፈስ ቅዱስ መልእክትማ ምንኛ እጅግ ክብር ሊደረግ ይገባ ይሆን? 9 ኵነኔን ለምታመጣ መልእክት ብዙ ክብር ከተደረገላት የጽድቅ መልእክትማ ምን ያህል ትከብርና ትመሰገን ይሆን? 10 በዚህ ፍጹም ክብር ባነጻጸሯት ጊዜ የከበረችው እንዳልከበረች ትሆናለችና። 11 ያ የሚያልፈው ክብር ካገኘ፥ ያ ጸንቶ የሚኖረውማ እንዴት እጅግ ክብር ያገኝ ይሆን? 12 እንግዲህ ይህን ያህል ተስፋ ካለን በግልጥ ፊት ለፊት ልንቀርብ እንችላለን። 13 የዚያን ይሻር የነበረውን መጨረሻ፥ የእስራኤል ልጆች እንዳያዩት ፊቱን ይሸፍን እንደ ነበረው እንደ ሙሴ አይደለም። 14 ነገር ግን እስከ ዛሬ ድረስ ልባቸው ተሸፍኖአል፤ ያም መጋረጃ ብሉይ ኪዳን በተነበበት ዘመን ሁሉ ጸንቶ ኖሮአል፤ ክርስቶስ እስኪያሳልፈው ድረስ አልተገለጠምና። 15 እስከ ዛሬም የሙሴን ሕግ ሲያነብቡ ያ መጋረጃ ልባቸውን ይሸፍናቸዋል። 16 ወደ እግዚአብሔር በተመለሱ ጊዜ ግን ያ መጋረጃ ከእነርሱ ይርቃል። 17 እግዚአብሔር መንፈስ ነውና፥ የእግዚአብሔር መንፈስ ባለበትም በዚያ ነፃነት አለ። 18 እኛስ ሁላችን ፊታችንን ገልጠን በመስተዋት እንደሚያይ የእግዚአብሔርን ክብር እናያለን፤ ከእግዚአብሔር መንፈስ እንደ ተሰጠን መጠን የእርሱን አርአያ እንመስል ዘንድ ከክብር ወደ ክብር እንገባለን። |