2 ቆሮንቶስ 12 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)ጳውሎስ ስላየው ራእይ 1 እነሆ መመካት ይቻለኛል፤ ነገር ግን አይጠቅምም፤ ደግሞም ወደ ጌታ ራእይና መገለጥ እሄዳለሁ። 2 በክርስቶስ ያመነ አንድ ሰው አውቃለሁ፤ ዘመኑ ከዐሥራ አራት ዓመት በፊት ነው፤ ነገር ግን በሥጋው ይሁን በነፍሱ እንጃ፥ እግዚአብሔር ያውቃል፤ ያን ሰው እስከ ሦስተኛው ሰማይ ድረስ ነጥቀው ወሰዱት። 3 ያን ሰው አውቀዋለሁ፤ በሥጋው ይሁን በነፍሱ እንጃ እግዚአብሔር ያውቃል። 4 ወደ ገነትም ነጥቀው ወሰዱት፤ በዚያም ሰው ሊናገረው የማይችለውን የማይተረጐም ነገር ሰማ። 5 ስለዚህም እንደዚህ ባለው እመካለሁ፤ በመከራዬ እንጂ በራሴስ አልመካም። 6 ልመካ ብሻም አላዋቂ አይደለሁም፤ እውነቱን እናገራለሁና፤ ነገር ግን ስላዩኝና ስለ ሰሙኝ እንደምበልጥ አድርገው እንዳይጠራጠሩኝ ትቸዋለሁ። 7 ስለዚህም ቢሆን በብዙ ራእይ እንዳልታበይ ሰውነቴን የሚወጋ እርሱም የሚጐስመኝ የሰይጣን መልእክተኛ ተሰጠኝ። 8 ስለዚህም ከእኔ ያርቀው ዘንድ ጌታዬን ሦስት ጊዜ ማለድሁት። 9 እርሱም፥ “ጸጋዬ ይበቃሀል፤ ኀይልስ በደዌ ያልቃል” አለኝ፤ የክርስቶስም ኀይል በእኔ ላይ ያድር ዘንድ በመከራዬ ልመካ ወደድሁ። 10 ስለዚህም ስለ ክርስቶስ መከራ መቀበልን፥ መሰደብን፥ መጨነቅን፥ መሰደድን፥ መቸገርንም ወደድሁ፤ መከራ በተቀበልሁ ጊዜ ወዲያውኑ እበረታለሁና። በቆሮንቶስ ሰዎች ላይ ስለ አደረገው ወቀሳ 11 እነሆ እናንተ ስላገበራችሁኝ በመመካቴ ሰነፍ ሆንሁ፤ ለእኔማ በእናንተ ዘንድ ልከብርና እናንተም ምስክሮች ልትሆኑኝ ይገባኝ ነበር፤ እኔ እንደ ኢምንት ብሆንም ዋናዎቹ ሐዋርያት ሁሉ ከሠሩት ሥራ ያጐደልሁባችሁ የለምና። 12 የሐዋርያት ምልክትስ በፍጹም ትዕግሥትና በተአምራት፥ ድንቅ ሥራ በመሥራትና በኀይላት ተደርጎላችኋል። 13 እከብድባችሁ ዘንድ ወደ እናንተ ካለመምጣቴ በቀር፥ ከአብያተ ክርስቲያናት ሁሉ ያሳነስኋችሁ በምንድን ነው? ይህቺን በደሌን ይቅር በሉኝ። 14 እነሆ ወደ እናንተ ልመጣ ስዘጋጅ ይህ ሦስተኛዬ ነው፤ ነገር ግን አልተፋጠንሁም ገንዘባችሁን ያይደለ፥ እናንተን እሻለሁና፤ ልጆች ለወላጆቻቸው ያይደለ ወላጆች ለልጆቻቸው ሊያከማቹ ይገባልና፤ 15 እኔ ግን እጥፍ ድርብ አወጣለሁ፤ ስለ ሕይወታችሁም ሰውነቴን አሳልፌ እሰጣለሁ፤ እናንተንም እጅግ ብወዳችሁ ራሴን ወደድሁ። 16 እኔ አልከበድሁባችሁም፤ ነገር ግን ምክር ዐዋቂ ሆኜ በመጠበብ ወሰድኋችሁ። 17 በውኑ ይህን አድርጉልኝ ብዬ ወደ እናንተ የላክሁት መልእክት አለን? ወይስ የቀማኋችሁ ነገር አለን? እንጃ። 18 እነሆ ቲቶን ማለድሁት፤ ከእርሱም ጋር ሌላውን ወንድማችንን ላክሁት፤ በውኑ ቲቶ የበደላችሁ በደል አለን? በእርሱ በአደረው መንፈስ የምንመላለስ፥ እርሱም የሄደበትን ፍለጋ የምንከተል አይደለንምን? 19 እኛስ ደግሞ ስለ ራሳችን የምንከራከራችሁ ይመስላችኋልን? በእግዚአብሔር ፊት በክርስቶስ ሆነን እንናገራለን፤ ወንድሞቻችን ሆይ፥ ይህ ሁሉ ግን እናንተ ትታነጹ ዘንድ ነው። 20 ነገር ግን ወደ እናንተ በመጣሁ ጊዜ እንደምወደው ሆናችሁ ያላገኘኋችሁ እንደ ሆነ፤ እኔም እንደማትወዱት እሆንባችኋለሁ ብዬ እፈራለሁ፤ ወይም እኮ በመካከላችሁ ክርክር፥ ኵራት፥ መቀናናት፥ መበሳጨት፥ መዘባበት፥ ወይም መተማማት፥ መታወክ፥ ወይም ልብን ማስታበይ ይኖር ይሆናል። 21 ወይም እንደ ገና ወደ እናንተ በመጣሁ ጊዜ በእናንተ ምክንያት እግዚአብሔር ያሳዝነኝ ይሆናል፤ በድለው ንስሓ ላልገቡም ስለ ርኵስነታቸውና ስለ መዳራታቸው፥ ስለሚሠሩት ዝሙታቸውም ለብዙዎች አዝን ይሆናል። |