ዘፍጥረት 5 - አዲሱ መደበኛ ትርጒምከአዳም እስከ ኖኅ 1 የተጻፈው የአዳም የትውልድ ሐረግ እንደሚከተለው ነው። እግዚአብሔር ሰውን ሲፈጥረው በራሱ አምሳል አበጀው፤ 2 ወንድና ሴት አድርጎ ፈጠራቸው። ባረካቸው፤ በተፈጠሩም ጊዜ “ሰው” ብሎ ጠራቸው፦ 3 አዳም፣ ዕድሜው 130 ዓመት በሆነ ጊዜ፣ እርሱን ራሱን የሚመስል ወንድ ልጅ ወለደ፤ ስሙንም ሴት ብሎ ጠራው። 4 ሴት ከተወለደም በኋላ፣ አዳም 800 ዓመት ኖረ፤ ሌሎች ወንዶችና ሴቶች ልጆችንም ወለደ፤ 5 አዳም በአጠቃላይ 930 ዓመት ከኖረ በኋላ ሞተ። 6 ሴት፣ ዕድሜው 105 ዓመት ሲሆን ሄኖስን ወለደ፤ 7 ሴት ሄኖስን ከወለደ በኋላ 807 ዓመት ኖረ፤ ሌሎች ወንዶችና ሴቶች ልጆችንም ወለደ። 8 ሴት በአጠቃላይ 912 ዓመት ከኖረ በኋላ ሞተ። 9 ሄኖስ፣ ዕድሜው 90 ዓመት በሆነ ጊዜ ቃይናንን ወለደ፤ 10 ሄኖስ ቃይናንን ከወለደ በኋላ 815 ዓመት ኖረ፤ ሌሎች ወንዶችና ሴቶች ልጆችንም ወለደ። 11 ሄኖስ በአጠቃላይ 905 ዓመት ከኖረ በኋላ ሞተ። 12 ቃይናን፣ ዕድሜው 70 ዓመት ሲሆን መላልኤልን ወለደ፤ 13 ቃይናን መላልኤልን ከወለደ በኋላ 840 ዓመት ኖረ፤ ሌሎች ወንዶችና ሴቶች ልጆችንም ወለደ። 14 ቃይናን በአጠቃላይ 910 ዓመት ከኖረ በኋላ ሞተ። 15 መላልኤል፣ ዕድሜው 65 ዓመት በሆነ ጊዜ ያሬድን ወለደ፤ 16 መላልኤል ያሬድን ከወለደ በኋላ 830 ዓመት ኖረ፤ ሌሎች ወንዶችና ሴቶች ልጆችንም ወለደ። 17 መላልኤል በአጠቃላይ 895 ዓመት ከኖረ በኋላ ሞተ። 18 ያሬድ፣ ዕድሜው 162 ዓመት ሲሆን ሔኖክን ወለደ፤ 19 ያሬድ ሔኖክን ከወለደ በኋላ 800 ዓመት ኖረ፤ ሌሎች ወንዶችና ሴቶች ልጆችንም ወለደ። 20 ያሬድ በአጠቃላይ 962 ዓመት ከኖረ በኋላ ሞተ። 21 ሔኖክ፣ ዕድሜው 65 ዓመት በሆነ ጊዜ ማቱሳላን ወለደ፤ 22 ሔኖክ ማቱሳላን ከወለደ በኋላ አካሄዱን ከእግዚአብሔር ጋራ በማድረግ 300 ዓመት ኖረ፤ ሌሎች ወንዶችና ሴቶች ልጆችንም ወለደ። 23 ሔኖክ በአጠቃላይ 365 ዓመት ኖረ፤ 24 ሔኖክ አካሄዱን ከእግዚአብሔር ጋራ አደረገ፤ እግዚአብሔር ስለ ወሰደውም አልተገኘም። 25 ማቱሳላ፣ ዕድሜው 187 ዓመት ሲሆን ላሜሕን ወለደ፤ 26 ማቱሳላ ላሜሕን ከወለደ በኋላ፣ 782 ዓመት ኖረ፤ ሌሎች ወንዶችና ሴቶች ልጆችንም ወለደ፤ 27 ማቱሳላ በአጠቃላይ 969 ዓመት ከኖረ በኋላ ሞተ። 28 ላሜሕ፣ ዕድሜው 182 ዓመት በሆነ ጊዜ፣ ልጅ ወለደ። 29 ስሙንም “እግዚአብሔር በረገማት ምድር ከልፋታችንና ከጕልበታችን ድካም ያሳርፈናል” ሲል ኖኅ ብሎ ጠራው። 30 ላሜሕ ኖኅን ከወለደ በኋላ፣ 595 ዓመት ኖረ፤ ሌሎች ወንዶችና ሴቶች ልጆችንም ወለደ። 31 ላሜሕ በአጠቃላይ 777 ዓመት ከኖረ በኋላ ሞተ። 32 ኖኅ ዕድሜው 500 ዓመት ሲሆን ሴምን፣ ካምንና ያፌትን ወለደ። |
መጽሐፍ ቅዱስ፣ አዲሱ መደበኛ ትርጕም™
የቅጂ መብት © 2001, 2024 በBiblica, Inc.
በፈቃድ የሚወሰድ። በዓለም ዐቀፍ ባለቤትነቱ።
The Holy Bible, New Amharic Standard Version™
Copyright © 2001, 2024 by Biblica, Inc.
Used with permission. All rights reserved worldwide.
Biblica, Inc.