Biblia Todo Logo
La Biblia Online

- Anuncios -


ሶፎንያስ 1 - አማርኛ አዲሱ መደበኛ ትርጉም


የእግዚአብሔር ፍርድ ቀን

1 ሶፎንያስ የኩሺ ልጅ ሲሆን፥ ኩሺ የገዳልያ ልጅ፥ ገዳልያ የአማርያ ልጅ፥ አማርያ ደግሞ የንጉሥ ሕዝቅያስ ልጅ ነው፤ የአሞን ልጅ ኢዮስያስ የይሁዳ ንጉሥ በነበረበት ዘመን እግዚአብሔር ለሰፎንያስ የተናገረው ትንቢት እንደሚከተለው ነው።

2 እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ “ሁሉን ነገር ከምድር ላይ ፈጽሜ አጠፋለሁ፤

3 ሰዎችንና እንስሶችን፥ የሰማይ ወፎችንና የባሕር ዓሣዎችን እደመስሳለሁ፤ ክፉዎች እንዲገለባበጡ አደርጋለሁ፤ የሰውን ዘር ከምድር ላይ አጠፋለሁ፤ ይህን የተናገርኩ እኔ እግዚአብሔር ነኝ።

4 “የኢየሩሳሌምንና የይሁዳን ሕዝብ ሁሉ እቀጣለሁ፤ ከዚያም ቦታ የበዓል አምልኮ ርዝራዥንና የጣዖት ካህናትን መታሰቢያ አጠፋለሁ።

5 ጣራ ላይ ወጥተው ለፀሐይ፥ ለጨረቃና ለከዋክብት የሚሰግዱትን አጠፋለሁ፤ እኔን እያመለኩና በስሜ እየማሉ፥ ዘወር ብለው ደግሞ ሚልኮም ተብሎ በሚጠራው ጣዖት ስም የሚምሉትን እደመስሳለሁ።

6 ከእኔ የራቁትን፥ እኔን መከተል የተዉትንና ወደ እኔም መጥተው እኔ እንድመራቸው ያልጠየቁኝን አጠፋለሁ።”

7 የእግዚአብሔር ፍርድ ቀን ስለ ቀረበ በእግዚአብሔር ፊት ዝም በሉ፤ እግዚአብሔር ሕዝቡን ለመሥዋዕት እንደሚታረድ እንስሳ አሳልፎ ለመስጠት እየተዘጋጀ ነው፤ ይሁዳን የሚበዘብዙ ጠላቶችንም ለይቶ አዘጋጅቶአል።

8 እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ “ሕዝቤን አሳልፌ በምሰጥበት ቀን ልዑላኑንና ባለ ሥልጣኖችን እንዲሁም የባዕድ ባህል የሚከተሉትን ሁሉ እቀጣለሁ።

9 በዚያን ቀን በአሕዛብ የአምልኮ ሥርዓት በቤተ መቅደሱ መድረክ ላይ እየዘለሉ የሚያመልኩትንና የጌታቸውን ቤት በዓመፅና በማታለል በተገኙ ዕቃዎች የሚሞሉትን ሰዎች እቀጣለሁ።”

10 እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ “በዚያን ቀን ከኢየሩሳሌም ቅጽር በዓሣ በር በኩል ኡኡታ ይሰማል፤ ከአዲሱም አደባባይ የዋይታ ድምፅ ያስተጋባል፤ በኰረብቶችም አካባቢ ከፍተኛ ሽብር ይሰማል።

11 እናንተ ከከተማው በታችኛው ክፍል የምትኖሩ ሁሉ ነጋዴዎቻችሁ ስለሚወገዱና በብር የሚነግዱ ሁሉ ስለሚጠፉ ይህን ድምፅ በምትሰሙበት ጊዜ ‘ዋይ! ዋይ!’ እያላችሁ አልቅሱ።

12 “በዚያን ቀን መብራት ይዤ ኢየሩሳሌምን እፈትሻለሁ፤ በመንደላቀቅ ኑሮ በአተላ ውስጥ አቅርሮ እንደ ቀረ የወይን ጠጅ የሆኑትንና ‘እግዚአብሔር በጎም ሆነ ክፉ ነገር አያደርግም’ የሚሉትን እቀጣለሁ።

13 ሀብታቸው ይዘረፋል፤ ቤቶቻቸውም ይፈርሳሉ፤ በዚያን ጊዜ ቤት ይሠራሉ፤ ነገር ግን አይኖሩበትም፤ ወይንም ይተክላሉ፤ ነገር ግን የወይኑን ጠጅ አይጠጡም።”

14 ታላቁ የእግዚአብሔር ቀን ቀርቦአል፤ አመጣጡም እየፈጠነ ነው፤ ያ ቀን እጅግ አስፈሪ ነው፤ በዚያን ቀን የሚሰማው ድምፅ አስከፊ ነው፤ ተዋጊው በከፍተኛ ድምፅ ይጮኻል።

15 ያ ዕለት የቊጣ፥ የመከራና የጭንቀት፥ የጥፋትና የመፍረስ፥ የጨለማና የጭጋግ፥ የደመናና የድቅድቅ ጨለማ ቀን ይሆናል፤

16 በዚያን ቀን በተመሸጉት ከተሞችና በረጃጅም ግንቦች ላይ የጦርነት መለከትና የማስጠንቀቂያ ድምፅ ይሰማል።

17 እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ “ኃጢአት በመሥራት እኔን ስለ በደሉ እንደ ዕውሮች እስኪደናበሩ ድረስ በሰዎች ላይ ታላቅ መከራ አመጣለሁ፤ ደማቸው እንደ ትቢያ ይፈስሳል፤ ሬሳቸውም እንደ ጒድፍ የትም ይጣላል።”

18 እግዚአብሔር ቊጣውን በሚገልጥበት በዚያን ቀን ሰዎችን ብራቸውና ወርቃቸው ሊያድናቸው አይችልም፤ እንደ እሳት ባለው ቅናቱ ምድር ሁሉ ትጠፋለች፤ ይህም የሚሆነው በዓለም የሚኖሩ ሰዎች ሁሉ በድንገት የሚያልቁ ስለ ሆነ ነው።

© The Bible Society of Ethiopia, 2005

© የኢትዮጵያ መጽሐፍ ቅዱስ ማኅበር፥ 1997

Bible Society of Ethiopia
Síguenos en:



Anuncios


¡Síguenos en WhatsApp! Síguenos