መዝሙር 28 - አማርኛ አዲሱ መደበኛ ትርጉም(የዳዊት መዝሙር) ርዳታ ለማግኘት የቀረበ ጸሎት 1 መከታዬ እግዚአብሔር ሆይ! ወደ አንተ ስጣራ ጩኸቴን ስማ! አንተ ካልሰማኸኝ ግን ወደ መቃብር ከሚወርዱት እንደ አንዱ መሆኔ ነው። 2 ወደ ተቀደሰው ቤተ መቅደስህ እጄን አንሥቼ ለእርዳታ በምጮኽበት ጊዜ እባክህ ጸሎቴን ስማኝ። 3 የክፋትን ሥራ ከሚሠሩ ክፉ ሰዎች ጋር አትውሰደኝ፤ እነርሱ ከጐረቤቶቻቸው ጋር በሰላም ይነጋገራሉ፤ በልባቸው ግን ተንኰል አለ። 4 ስለ ፈጸሙት በደል ተገቢ ዋጋቸውን ክፈላቸው፤ በእጃቸው ስለ ፈጸሙት ክፉ ሥራ ፍረድባቸው፤ ተገቢ ቅጣታቸውንም ስጣቸው። 5 እነርሱ ለእግዚአብሔር አድራጎትና ለእጁ ሥራ ትኲረት ስለማይሰጡ እርሱ ይሰባብራቸዋል፤ እንደገናም አይገነባቸውም። 6 የልመናዬን ድምፅ ስለ ሰማኝ እግዚአብሔር የተመሰገነ ይሁን። 7 እግዚአብሔር ኀይሌና ጋሻዬ ነው፤ ስለሚረዳኝና ደስ ስለሚያሰኘኝም በእርሱ እተማመናለሁ፤ በመዝሙሮቼም አመሰግነዋለሁ። 8 እግዚአብሔር ለሕዝቡ ኀይላቸው ነው፤ ቀብቶ ላነገሠው ንጉሥም የመዳኛ ከለላው ነው። 9 አምላክ ሆይ! ሕዝብህን አድን፤ የአንተ የሆኑትንም ባርክ፤ እረኛቸውም ሁን፤ ለዘለዓለምም ተንከባከባቸው። |