መዝሙር 148 - አማርኛ አዲሱ መደበኛ ትርጉምፍጥረቶች ሁሉ እግዚአብሔርን ያመስግኑ 1 እግዚአብሔርን አመስግኑ! ከላይ ከሰማያት አመስግኑት። 2 እናንተ የእርሱ መላእክት ሁሉ አመስግኑት፤ በሰማይ ያላችሁ ሠራዊቱ ሁሉ አመስግኑት። 3 ፀሐይና ጨረቃ አመስግኑት። የምትበሩ ከዋክብት ሁሉ አመስግኑት፤ 4 ከፍተኞች ሰማያት አመስግኑት፤ ከጠፈር በላይ ያላችሁ ውሃዎችም አመስግኑት። 5 ሁሉም የእግዚአብሔርን ስም ያመስግኑ! እርሱ አዘዘ እነርሱም ተፈጠሩ። 6 ምንጊዜም በማይፈርስ ድንጋጌ ለዘለዓለም እስከ ዘለዓለም መሥርቶአቸዋል። 7 የባሕር አራዊትና የውቅያኖስ ጥልቀቶች እግዚአብሔርን ከምድር አመስግኑ። 8 እሳትና በረዶ፥ ዐመዳይና ደመና፥ ትእዛዙን የምትፈጽሙም ብርቱዎች ነፋሳት እግዚአብሔርን አመስግኑ። 9 ኰረብቶችና ተራራዎች፥ የፍሬ ተክሎችና የደን ዛፎች ሁሉ አመስግኑት። 10 አራዊትና ለማዳ እንስሶች፥ በምድር የምትሳቡና በክንፍ የምትበርሩ ፍጥረቶች ሁሉ እግዚአብሔርን አመስግኑት። 11 ነገሥታትና የምድር ሕዝቦች፥ መሳፍንትና ፈራጆች ሁሉ አመስግኑት። 12 ጐልማሶችና ልጃገረዶች፥ ሽማግሌዎችና ልጆች ሁሉ አመስግኑት። 13 የእርሱ ስም ከሌሎች ስሞች ስለሚበልጥና ክብሩም ከምድርና ከሰማይ በላይ ከፍ ያለ ስለ ሆነ ሁሉም የእግዚአብሔርን ስም ያመስግኑ! 14 ለእርሱ ቅርብ የሆኑትን ታማኝ አገልጋዮቹን እስራኤልን ከፍ ከፍ አደረጋቸው፤ ምስጋናንም አቀዳጃቸው። እግዚአብሔርን አመስግኑ! |