Biblia Todo Logo
La Biblia Online
- Anuncios -


ዘኍል 13 - አማርኛ አዲሱ መደበኛ ትርጉም


የከነዓንን ምድር እንዲመረምሩ የተላኩ ሰላዮች
( ዘዳ. 1፥19-33 )

1 እግዚአብሔር ሙሴን እንዲህ አለው፤

2 “ከዐሥራ ሁለቱ የእስራኤል ነገዶች አንዳንድ የሕዝብ መሪዎችን መርጠህ፥ እኔ ለእስራኤላውያን ወደምሰጣት ወደ ከነዓን ምድር ሄደው የምድሪቱን ሁኔታ መርምረው እንዲመለሱ ላካቸው፤”

3 ሙሴም በእግዚአብሔር ትእዛዝ መሠረት ከእስራኤል መሪዎች መካከል ከፋራን ምድረ በዳ ዐሥራ ሁለት ሰዎችን ላከ።

4 ስማቸው እንደሚከተለው ነበር፤ ከሮቤል ነገድ የዛኩር ልጅ ሻሙዓ፥

5 ከስምዖን ነገድ የሖሪ ልጅ ሣፋጥ፥

6 ከይሁዳ ነገድ የይፉኔ ልጅ ካሌብ፥

7 ከይሳኮር ነገድ የዮሴፍ ልጅ ይግአል፥

8 ከኤፍሬም ነገድ የነዌ ልጅ ሆሼዓ

9 ከብንያም ነገድ የራፉ ልጅ ፈልጢ፥

10 ከዛብሎን ነገድ የሶዲ ልጅ ጋዱኤል፥

11 ከዮሴፍ ነገድ (እርሱም ከምናሴ ነገድ) የሱሲ ልጅ ጋዲ፥

12 ከዳን ነገድ የገማሊ ልጅ ዓሚኤል፥

13 ከአሴር ነገድ የሚካኤል ልጅ ሰቱር፥

14 ከንፍታሌም ነገድ የዋፍሲ ልጅ ናሕቢ፥

15 ከጋድ ነገድ የማኪ ልጅ ገኡኤል።

16 እንግዲህ የአገሪቱን ሁኔታ አጥንተው እንዲመለሱ ሙሴ የላካቸው ሰዎች እነዚህ ነበሩ፤ የነዌን ልጅ ሆሼዓን “ኢያሱ” ብሎ ስሙን ለወጠው።

17 ሙሴም ሲልካቸው እንዲህ አላቸው፦ “በኔጌብ በኩል አድርጋችሁ ወደ ተራራማው አገር ውጡ።

18 አገሪቱ ምን እንደምትመስል፥ ምን ያኽል ሕዝብ እንደሚኖርባትና የሕዝቡም ብርታት ምን ያኽል እንደ ሆነ መርምሩ፤

19 ምድሪቱ መልካም ወይም መጥፎ እንደ ሆነች፥ ሕዝቡም የሚኖሩት ግልጥ በሆኑ መንደሮች ወይም በተመሸጉ ከተሞች እንደ ሆነ አጥኑ።

20 አፈሩ ለም፥ ምድሪቱም በደን የተሸፈነች መሆንዋን መርምሩ፤ አይዞአችሁ እዚያ ከሚገኘው ፍራፍሬ ይዛችሁ ኑ።” ወቅቱም የወይን ፍሬ መብሰል የጀመረበት ጊዜ ነበር።

21 ስለዚህ ሰዎቹ ወደ ሰሜን ሄዱ፤ በአገሪቱም ከሚገኘው ከጺን ምድረ በዳ ጀምረው ለሐማት መተላለፊያ ቅርብ እስከሆነው ረሖብ ድረስ አጠኑ።

22 በመጀመሪያው ወደ ኔጌብ ሄደው ወደ ኬብሮን መጡ፤ ይህችም ኬብሮን “ዐናቂም” ተብለው የሚጠሩ የግዙፋን ሰዎች ዘር የሆኑ አሒማን፥ ሼሻይ እና ታልማይ የሚባሉት ጐሣዎች መኖሪያ ነበረች። (ኬብሮን የተመሠረተችውም በግብጽ ምድር ጾዓን ተብላ የምትጠራው ከተማ ከመቈርቈርዋ ሰባት ዓመት ቀደም ብሎ ነበር።)

23 አልፈውም ወደ ኤሾኮል ሸለቆ ደረሱ፤ ከዚያም የወይን ዘለላ ያለበትን ቅርንጫፍ ቈረጡ፤ ያንንም የወይን ዘለላ አንድ ሰው ብቻውን ሊሸከመው የማይችል ከባድ ከመሆኑ የተነሣ ሁለት ሰዎች በመሎጊያ በትከሻቸው ላይ ተሸከሙት፤ ከዚህም ጋር የሮማንና የበለስ ፍሬ ይዘው መጡ።

24 ያ ቦታ “የኤሽኮል ሸለቆ” ተብሎ የተጠራበትም ምክንያት እስራኤላውያን የወይን ፍሬ ዘለላ ቈርጠው ያመጡበት ስፍራ ስለ ነበር ነው።

25 ሰዎቹ ምድሪቱን ለአርባ ቀኖች ካጠኑ በኋላ ተመለሱ።

26 በፋራን ምድረ በዳ በቃዴስ ወደነበሩት ወደ ሙሴና አሮን ወደ መላውም የእስራኤል ማኅበር መጡ፤ እነርሱም ያዩትን ነገር ሁሉ አስረዱ፤ ያመጡትንም ፍሬ አሳዩአቸው፤

27 ለሙሴም እንዲህ ብለው ነገሩት፦ “ምድሪቱን አጥንተን በእርግጥም በማርና በወተት የበለጸገች አገር መሆንዋን ተረድተናል፤ ምድሪቱም የምታፈራው ፍሬ ዐይነት ይህ ነው፤

28 ነገር ግን በዚያች ምድር የሚኖሩ ሕዝብ እጅግ ብርቱዎች ናቸው፤ ከተሞቻቸውም ታላላቆችና የተመሸጉ ናቸው፤ ከዚህም ሁሉ በላይ እጅግ ግዙፋን የዐናቅ ዘሮች አይተናል።

29 ዐማሌቃውያን በኔጌብ ምድር የሚኖሩ ሲሆን፥ ሒታውያን፥ ኢያቡሳውያንና አሞራውያን በተራራማው አገር፥ ከነዓናውያን ደግሞ በዮርዳኖስ ወንዝ ዳርና በሜዲቴራኒያን በባሕር ዳር ይኖራሉ።”

30 ካሌብ ግን በሙሴ ፊት ሕዝቡን ጸጥ በማሰኘት “እነርሱን ድል ለመንሣት የሚያስችል በቂ ኀይል ስለ አለን አገሪቱን አሁኑኑ ሄደን እንያዛት አለ።”

31 ከካሌብ ጋር ሄደው የነበሩት ሰዎች ግን “እኛ በእነርሱ ላይ አደጋ ለመጣል ከቶ ኀይል የለንም፤ በዚያ የሚኖሩት ሰዎች ከእኛ ይበልጥ ብርቱዎች ናቸው” ብለው ተናገሩ።

32 ሊሰልሉ ስለ ሄዱበት አገርም ለእስራኤላውያን ያቀረቡት ዘገባ ተስፋ አስቈራጭ ነበር፥ እነርሱም፥ “ልንሰልል የሄድንበት አገር ወደ እርስዋ ለመኖር የሚመጣውን ሰው የምትውጥ ናት፤ እዚያ ያየናቸው ሰዎች ረጃጅሞች ናቸው።

33 በዚያም ከኔፊሊም ወገን የሆኑትን የዐናቅን ዘሮች አይተናል፤ እኛ በእነርሱ ፊት ልክ እንደ ፌንጣ ያኽል ሆነን ነበር የታየነው፤ እነርሱም እንደዚያው አድርገው ሳይመለከቱን አይቀሩም” አሉ።

© The Bible Society of Ethiopia, 2005

© የኢትዮጵያ መጽሐፍ ቅዱስ ማኅበር፥ 1997

Bible Society of Ethiopia
Síguenos en:



Anuncios


¡Síguenos en WhatsApp! Síguenos