ዘፀአት 2 - አማርኛ አዲሱ መደበኛ ትርጉምየሙሴ መወለድ 1 በዚያን ጊዜ ከሌዊ ነገድ የሆነ አንድ ሰው አንዲት ሌዋዊት ሴት አገባ፤ 2 እርስዋም ወንድ ልጅ ወለደችለት፤ ሕፃኑ መልከ መልካም መሆኑን አይታ ሦስት ወር ሸሸገችው። 3 ሆኖም ከዚያ በላይ ልትሸሽገው አለመቻልዋን በተረዳች ጊዜ፥ በሣጥን መልክ ከደንገል የተሠራ ቅርጫት አዘጋጀች፤ ውሃም እንዳያስገባ በቅጥራን ለቀለቀችው፤ ሕፃኑንም አስገብታ ቅርጫቱን በወንዝ ዳር በሚገኝ ቀጤማ መካከል አስቀመጠችው። 4 የሕፃኑም እኅት የሚደርስበትን ነገር ለማየት ራቅ ብላ ትጠባበቀው ነበር። 5 በዚህ ጊዜ የንጉሡ ሴት ልጅ ልትታጠብ ወደ ወንዝ ወረደች፤ ሴቶች አገልጋዮችዋም በወንዙ ዳር ይሄዱ ነበር፤ እርስዋም በቀጤማ መካከል የተቀመጠ አንድ ቅርጫት አየች፤ አገልጋይዋንም ልካ አስመጣችው። 6 በከፈተችውም ጊዜ አንድ ሕፃን በውስጡ አገኘች፤ ሕፃኑም ያለቅስ ስለ ነበር አዘነችለትና “ይህ ከዕብራውያን ሕፃናት አንዱ ነው” አለች። 7 በዚያን ጊዜ የሕፃኑ እኅት የንጉሡን ልጅ “ይህን ሕፃን እያጠባች የምታሳድግልሽ ከዕብራውያን ሴቶች አንዲት ሞግዚት ልጥራልሽን?” ስትል ጠየቀቻት። 8 “አዎ፥ ሄደሽ ጥሪልኝ” ስላለቻት ልጅቱ ሄደች፤ የሕፃኑንም እናት ጠርታ አመጣች። 9 የንጉሡ ልጅም ሴትዮይቱን “ይህን ሕፃን ወስደሽ እያጠባሽ አሳድጊልኝ፤ ደመወዝሽንም እከፍልሻለሁ” አለቻት፤ ስለዚህ ሴቲቱ ሕፃኑን ወስዳ ታጠባው ጀመር። 10 ሕፃኑም ባደገ ጊዜ ወደ ንጉሡ ልጅ አመጣችው፤ የእርስዋም ልጅ ተባለ። እርስዋም “ከውሃ ያወጣሁት ስለ ሆነ ስሙ ሙሴ ተብሎ ይጠራ” አለች። የሙሴ ወደ ምድያም መኰብለል 11 ሙሴ ባደገ ጊዜ ወገኖቹን ለመጐብኘት ሄደ፤ ከባድ ሥራ መሥራታቸውን ተመለከተ፤ እንዲያውም አንድ ግብጻዊ ከወገኖቹ አንዱ የሆነውን ዕብራዊ ሲደበድብ አየ። 12 ሙሴ ዙሪያውን ተመልክቶ ማንም እንደማያየው ከተረዳ በኋላ ግብጻዊውን ገድሎ በአሸዋ ውስጥ ደበቀው። 13 በማግስቱም ወደዚያው ስፍራ ተመልሶ ሲሄድ ሁለት ዕብራውያን እርስ በርሳቸው ሲጣሉ አየ፤ በደል የሠራውንም ሰው ተመልክቶ “ወገንህ የሆነውን ዕብራዊ ለምን ትመታዋለህ?” ሲል ጠየቀው። 14 ሰውየውም “አንተን በእኛ ላይ ገዢና ዳኛ አድርጎ የሾመህ ማን ነው? ወይስ ያንን ግብጻዊ እንደ ገደልክ እኔንም መግደል ትፈልጋለህን?” አለው፤ ሙሴም እጅግ ፈርቶ “ያደረግኹት ነገር ታውቋል ማለት ነው” ብሎ አሰበ። 15 ንጉሡም የሆነውን ነገር ሁሉ በሰማ ጊዜ ሙሴን ለማስገደል ፈለገ፤ ሙሴ ግን ኰብልሎ በዚያው ለመኖር ወደ ምድያም አገር ሄደ። እዚያም እንደ ደረሰ በውሃ ጒድጓድ አጠገብ ተቀመጠ፤ 16 አንድ የምድያም ካህን ሰባት ሴቶች ልጆች ነበሩት፤ እነርሱም ውሃ ለመቅዳትና በገንዳ እየሞሉ የአባታቸውን በጎችና ፍየሎች ለማጠጣት ወደዚያ መጡ። 17 እረኞችም መጥተው እነዚያን ሴቶች አባረሩአቸው፤ ሙሴም ሴቶቹን ከእረኞቹ እጅ በማዳን መንጋቸውን ውሃ አጠጣላቸው። 18 እነዚያም ሴቶች ልጆች ወደ አባታቸው ወደ ራጉኤል በተመለሱ ጊዜ “ዛሬ እንዴት በፍጥነት ተመለሳችሁ?” ሲል ጠየቃቸው። 19 እነርሱም “አንድ ግብጻዊ ከእረኞች እጅ አዳነን፤ እንዲያውም ውሃ እየቀዳ መንጋችንን አጠጣልን” ብለው መለሱለት። 20 አባታቸውም “ታዲያ፥ አሁን ሰውየው የት ነው? ለምንስ ተዋችሁት? ሂዱ ጥሩትና መጥቶ እህል ይቅመስ” አላቸው። 21 ሙሴም ከዚያ ሰው ጋር ለመኖር ፈቃደኛ ሆነ፤ ያም ሰው ልጁን ጺጳራን ሚስት ትሆነው ዘንድ ለሙሴ ሰጠው። 22 እርስዋም ወንድ ልጅ ወለደችለት፤ ሙሴም “እኔ በዚህ ምድር መጻተኛ ነኝ” ሲል ልጁን ጌርሾም ብሎ ጠራው። 23 ከብዙ ዓመቶች በኋላ የግብጽ ንጉሥ ሞተ፤ እስራኤላውያን ግን አሁንም በባርነት ቀንበር ሥር በመጨነቅ ርዳታ ለማግኘት በመጮኽ ላይ ነበሩ፤ ጩኸታቸውም ወደ እግዚአብሔር ደረሰ። 24 ጭንቀት የተሞላበትን ጩኸታቸውንም ሰምቶ እግዚአብሔር ከአብርሃም፥ ከይስሐቅና ከያዕቆብ ጋር የገባውን ቃል ኪዳን አስታወሰ። 25 እግዚአብሔር እስራኤላውያን በባርነት መጨነቃቸውን አይቶ ስለ እነርሱ አሰበ። |