መሳፍንት 13 - መጽሐፍ ቅዱስ - (ካቶሊካዊ እትም - ኤማሁስ)የሳምሶን መወለድ 1 እስራኤላውያን እንደገና በጌታ ፊት ክፉ ድርጊት ፈጸሙ፤ ስለዚህም ጌታ በፍልስጥኤማውያን እጅ አርባ ዓመት እንዲገዙ አሳልፎ ሰጣቸው። 2 ማኑሄ የተባለ ከዳን ወገን የተወለደ አንድ የጾርዓ ሰው ነበረ፤ ሚስተ መካን ስለ ነበረች ልጅ አልወለደችም። 3 የጌታም መልአክ ለሴቲቱ ተገልጦ እንዲህ አላት፤ “እነሆ፤ አንቺ መካን ነሽ፤ ልጅም አልወለድሽም፤ ነገር ግን ትፀንሻለሽ ወንድ ልጅም ትወልጃለሽ። 4 እንግዲህ ተጠንቀቂ፤ የወይን ጠጅም ሆነ ሌላ የሚያሰክር መጠጥ አትጠጪ፤ ርኩስ ነገርም አትብይ፤ 5 ምክንያቱም ትፀንሻለሽ፤ ወንድ ልጅም ትወልጃለሽ። በራሱ ላይ ምላጭ አይድረስበት፤ ልጁ ከእናቱ ማሕፀን ጀምሮ ናዝራዊ በመሆን ለእግዚአብሔር የተለየ ይሆናልና፤ እስራኤልንም ከፍልስጥኤማውያን እጅ መታደግ ይጀምራል።” 6 ከዚያም ሴቲቱ ወደ ባሏ ሄዳ እንዲህ አለችው፤ “የእግዚአብሔር ሰው ወደ እኔ መጣ፤ የእግዚአብሔር መልአክ የሚመስልና እጅግ የሚያስደነግጥ ነበር። ከየት እንደመጣ አልጠየቅሁትም፤ እርሱም ስሙን አልነገረኝም፤ 7 ነገር ግን፥ ‘ትፀንሻለሽ፤ ወንድ ልጅም ትወልጃለሽ፤ ስለዚህ ከእንግዲህ ወዲያ የወይን ጠጅም ሆነ ሌላ የሚያሰክር መጠጥ አትጠጪ፤ ርኩስ ነገር አትብይ፤ ልጁም ከእናቱ ማሕፀን ጀምሮ እስኪሞት ድረስ ናዝራዊ በመሆን ለእግዚአብሔር የተለየ ይሆናልና’ ብሎኛል።” የመልአኩ ለሁለተኛ ጊዜ መታየት 8 ከዚያም ማኑሄ፥ “ጌታ ሆይ፥ የሚወለደውን ልጅ እንዴት አድርገን ማሳደግ አንዳለብን እንዲያስተምረን ያ ወደኛ የላከው የእግዚአብሔር ሰው እንደገና እንዲመጣ እለምንሃለሁ” ብሎ ወደ ጌታ ጸለየ። 9 እግዚአብሔርም የማኑሄን ጸሎት ሰማ፤ የእግዚአብሔርም መልአክ ሴቲቱ በዕርሻ ውስጥ ሳለች ተገለጠላት፤ በዚህ ጊዜ ግን ባሏ ማኑሄ አብሮአት አልነበረም። 10 እርሷም ለባሏ ለመንገር ፈጥና በመሄድ፥ “ባለፈው ጊዜ የተገለጠልኝ ሰው ዛሬም ተገለጠልኝ” አለችው። 11 ማኑሄም ተነሥቶ ሚስቱን ተከተላት፤ ሰውየው እንደደረሰም፥ “ከሚስቴ ጋር ተነጋግረህ የነበርኸው አንተ ነህ?” ሲል ጠየቀው። እርሱም፤ “አዎን እኔ ነኝ” አለው። 12 ማኑሄም፥ “ያልከው በሚፈጸምበት ጊዜ የልጁ ሕይወት የሚመራው እንዴት ነው? እኛስ ምን ማድረግ አለብን?” ሲል ጠየቀው። 13 የጌታም መልአክ እንዲህ አለው፤ “ሚስትህ የነገርኋትን ሁሉ ታድርግ። 14 ከወይን ተክል የሚገኝ ማንኛውንም ነገር አትብላ፤ የወይን ጠጅም ሆነ ሌላ የሚያሰክር መጠጥ አትጠጣ፤ ርኩስ ነገር አትብላ፤ እኔ ያዘዝኳትን ሁሉ ታድርግ።” 15 ከዚያም ማኑሄ የጌታን መልአክ “የፍየል ጠቦት ዐርደን እስክናዘጋጅልህ ድረስ እባክህ ቈይ” አለው። 16 የጌታም መልአክ፥ “የግድ ብታቈየኝ እንኳ የምታቀርበውን ማንኛውንም ምግብ አልበላም፤ ነገር ግን የሚቃጠል መሥዋዕት የምታዘጋጅ ከሆነ እርሱን ለጌታ አቅርበው” አለው። የሚያነጋግረው የጌታ መልአክ መሆኑን አላወቀም ነበር። 17 ማኑሄ የጌታን መልአክ፥ “የተናገርከው ሲፈጸም እንድናከብርህ ስምህ ማን ነው?” በማለት ጠየቀው። 18 የጌታም መልአክ፥ “ስሜ ድንቅ ስለ ሆነ፥ ለምን ትጠይቀኛለህ?” አለው። 19 ማኑሄም የፍየሉን ጠቦት ከእህል ቁርባኑ ጋር ወስዶ በዐለት ላይ ለጌታ ሠዋው። ማኑሄና ሚስቱ እያዩ ጌታ አስደናቂ ነገር አደረገ፤ 20 የእሳቱ ነበልባል ከመሠዊያው ወደ ሰማይ ሲወጣ፥ የጌታ መልአክ በነበልባሉ ውስጥ ዐረገ። ማኑሄና ሚስቱ ይህን ሲመለከቱ በግንባራቸው መሬት ላይ ተደፉ። 21 የጌታም መልአክ ለማኑሄና ለሚስቱ ዳግመኛ ባለመገለጡ፥ ቀደም ሲል የተገለጠላቸው የጌታ መልአክ መሆኑን ማኑሄ ዐወቀ። 22 ሚስቱንም፥ “እግዚአብሔርን ስላየን ያለ ጥርጥር እንሞታለን” አላት። 23 ሚስቱ ግን መልሳ እንዲህ አለችው፥ “ጌታ ሊገድለን ቢፈልግ ኖሮ፥ የሚቃጠለውን መሥዋትና የእህል ቁርባኑን ከእጃችን ባልተቀበለን፤ ደግሞም ይህን ነገር ሁሉ ባላሳየንና እንዲህ ያለውንም ነገር በዚህ ጊዜ ባልነገረን ነበር።” 24 ሴቲቱ ወንድ ልጅ ወለደች፤ ስሙንም ሳምሶን ብላ ጠራችው፤ ልጁ አደገ፤ ጌታም ባረከው፤ 25 የጌታም መንፈስ በጾርዓና በኤሽታኦል መካከል ባለው በዳን ሰፈር ሳለ ያነቃቃው ጀመር። |