ኢዮብ 9 - መጽሐፍ ቅዱስ - (ካቶሊካዊ እትም - ኤማሁስ)1 ኢዮብም መለሰ፤ እንዲህም አለ፦ 2 “በእውነት እንዲህ እንደሆነ አወቅሁ፥ ሰውስ በእግዚአብሔር ፊት ጻድቅ መሆን እንዴት ይችላል? 3 ከእርሱ ጋር መከራከር ቢፈልግ፥ ከሺህ ነገር አንዱን መመለስ አይችልም። 4 ልቡ ጠቢብ፥ ኃይሉም ታላቅ ነው፥ እርሱንስ ተዳፍሮ በደኅና የቆየ ማን ነው? 5 ተራሮችን ይነቅላል፥ ነገር ግን አያውቁትም፥ በቁጣውም ይገለብጣቸዋል። 6 ምድርን ከስፍራዋ ያናውጣታል፥ ምሰሶችዋም ይንቀጠቀጣሉ። 7 ፀሐይን ያዝዛታል፥ አትወጣምም፥ ከዋክብትንም ያትማል። 8 ሰማያትን ብቻውን ይዘረጋል፥ በባሕሩም ማዕበል ላይ ይረግጣል። 9 ድብ የሚባለውን እና ኦሪዮን የሚባለውን ኮከብ፥ ሰባቱንም ከዋክብት፥ በደቡብም በኩል ያሉትን የከዋክብት ማደሪያዎች ሠርቶአል። 10 የማይመረመረውን ታላላቅ ነገር፥ የማይቈጠረውንም ተአምራት ያደርጋል። 11 እነሆ፥ ቢመጣብኝ አላየውም፥ ቢያልፍብኝም አላውቀውም። 12 እነሆ፥ ፈጥኖ ቢነጥቅ የሚከለክለው ማን ነው? እርሱንስ፦ ምን ታደርጋለህ? የሚለው ማን ነው?” 13 “እግዚአብሔር ቁጣውን አይመልስም፥ ከእርሱ በታች ረዓብን የሚረዱ ይዋረዳሉ። 14 ይልቁንስ እመልስለት ዘንድ፥ ቃሌንስ በፊቱ እመርጥ ዘንድ እኔ ማን ነኝ? 15 ጻድቅ ብሆንም እንኳን ልመልስለት አልችልም፥ ፈራጄን እማጸናለሁ እንጂ። 16 ብጠራው እርሱም ቢመልስልኝ ኖሮ፥ ቃሌን ሰማ ብዬ አላምንም ነበር። 17 በዐውሎ ነፋስ ይሰብረኛል፥ ቁስሌንም ያለ ምክንያት ያበዛል። 18 እተነፍስ ዘንድ አይተወኝም፥ ነገር ግን መራራን ነገር አጥግቦኛል። 19 የኃይል ነገር ከሆነ፥ ኃያሉ እርሱ እነሆ፥ የፍርድ ነገር ከሆነም፥ የችሎቱን ጊዜ ወሳኙ ማን ነው? ይላል። 20 ጻድቅ ብሆን እንኳን አፌ ይወቅሰኛል፥ ፍጹምም ብሆን ጠማማ ያደርገኛል። 21 ፍጹም ነኝ ራሴንም አልመለከትም፥ ሕይወቴንም እንቃታለሁ። 22 ይህ ሁሉ አንድ ነው፥ ስለዚህ፦ ፍጹማንንና ክፉዎችን ያጠፋል እላለሁ። 23 መቅሠፍቱ ፈጥኖ ቢገድል፥ በንጹሐን ፈተና ይሳለቃል። 24 ምድር በኃጥአን እጅ ተሰጥታለች፥ የፈራጆችዋን ፊት ሸፍኖአል፥ ይህንን ያደረገው እርሱ ካልሆነ ሌላ ማን ነው?” 25 “ቀኖቼ ከሚሮጥ ሰው ይልቅ ይፈጥናሉ፥ ይሸሻሉ፥ መልካምንም አያዩም። 26 የደንገል ታንኳ እንደሚፈጥን፥ ንስርም ወደ ንጥቂያው እንደሚበርር ያልፋሉ። 27 እኔ፦ የኀዘን እንጉርጉሮዬን እረሳለሁ፥ ፊቴን መልሼ እጽናናለሁ ብል፥ 28 ንጹሕ እንደማታደርገኝ እኔ አውቃለሁና ከመከራዬ ሁሉ የተነሣ እፈራለሁ። 29 በደለኛ እሆናለሁ፥ ስለ ምንስ በከንቱ እደክማለሁ? 30 በአመዳይ ውስጥ ብታጠብ፥ እጆቼንም እጅግ ባነጻ፥ 31 በአዘቅት ውስጥ ታሰጥመኛለህ፥ ልብሴም ይጸየፈኛል። 32 እንድመልስለት አብረን ወደ ፍርድ እንገባ ዘንድ፥ እርሱ እንደ እኔ ሰው አይደለም። 33 እጁን በሁለታችን ላይ የሚያኖር ዳኛ በመካከላችን ምነው በተገኘ! 34 በትሩን ከእኔ ላይ ያርቅ፥ ግርማውም አያስፈራኝ፥ 35 እናገርም ነበር፥ አልፈራውምም ነበር፥ በራሴ እንዲህ አይደለሁምና።” |