Biblia Todo Logo
La Biblia Online
- Anuncios -


ኢዮብ 15 - መጽሐፍ ቅዱስ - (ካቶሊካዊ እትም - ኤማሁስ)

1 ቴማናዊውም ኤልፋዝ መለሰ፤ እንዲህም አለ፦

2 “በውኑ ጠቢብ ሰው እንደ ነፋስ በሆነ እውቀት ይመልሳልን? ሆዱንስ በምሥራቅ ነፋስ ይሞላልን?

3 ከማይረባ ነገር፥ ወይስ ከማይጠቅም ንግግር ጋር ይዋቀሳልን?

4 አንተም ፈሪሃ እግዚአብሔርን እስከ መተው ደርሰሃል፥ በእግዚአብሔርም ፊት አምልኮን ታስቀራለህ።

5 በደልህ ንግግርህን ይመራዋል፥ የተንኰለኞችንም አንደበት ትመርጣለህ።

6 የሚፈርድብህ አፍህ ነው እንጂ እኔ አይደለሁም፥ ከንፈሮችህም ይመሰክሩብሃል።”

7 “በውኑ መጀመሪያ የተወለደው የሰው ልጅ አንተ ነህን? ከተራሮች በፊትስ ተፀንሰሀልን?

8 የእግዚአብሔርንስ ምሥጢር ሰምተሃልን? ጥበብን የግልህ ለማድረግ ትመኛለህን?

9 እኛ ሳናውቀው አንተ የምታወቀው ምንድነው? ከእኛ ዘንድስ ሳይኖር የምታስተውለው ምንድነው?

10 በዕድሜ ከአባትህ የሚበልጡ ሽበትም ያላቸው ሽማግሌዎችም ከእኛ ጋር አሉ።

11 በውኑ የእግዚአብሔር ማጽናናት፥ በየውሃትም የተነገረህ ቃል ጥቂት ነውን?

12 ልብህስ ለምን ወደ ሌላ ይወስድሃል? ዐይኖችህስ ለምን ይገላምጣሉ?

13 ቁጣህን በእግዚአብሔር ላይ እስከ ማንሣት ደርሰህ፥ እነኚህንም ቃላት ከአፍህ እስከ ማውጣት ደርሰህ።

14 ከንጹሕ ለመመደብ የሰው ልጅ ምንድነው? ጻድቅስ ለመባል ከሴት የተወለደ ምንድነው?

15 እነሆ፥ ቅዱሳኑን እንኳን አያምናቸውም፥ ሰማያትም በፊቱ ንጹሐን አይደሉም።

16 ታዲያ አስጸያፊና የረከሰ፥ በደልን እንደ ውኃ የሚጠጣ ሰው ምንኛ ያንስ?!”

17 “ስማኝ ልንገርህ፥ እነሆም ያየሁትን ልተርክልህ፤

18 ጠቢባን የተናገሩትን፥ አባቶቻቸውም ያልሰወሩትን፤

19 ምድሪቱ ለእነርሱ ብቻ ተሰጥታለችና፥ በመካከላቸውም እንግዳ አልገባባቸውም።

20 ክፉ ሰው ዕድሜ ልኩን ሲሠቃይ ይኖራል፥ እንዲሁም ግፈኛ በተመደቡለት ዓመታት በሙሉ።

21 የሚያስደነግጥ ድምፅ በጆሮው ነው፥ በሰላምም ሳለ ቀማኛ ይመጣበታል።

22 ከጨለማ ተመልሼ እወጣለሁ ብሎ አያምንም፥ ሰይፍም ይሸመቅበታል።

23 ተቅበዝብዞም፦ ወዴት አለ? እያለ እንጀራ ይለምናል፥ የጨለማ ቀን እንደ ቀረበበት ያውቃል።

24 መከራና ጭንቀት ያስፈራሩታል፥ ለጦርነት እንደ ተዘጋጀ ንጉሥ ያሸንፉታል።

25 እጁን በእግዚአብሔር ላይ ዘርግቶአልና፥ ሁሉን የሚችል አምላክን ደፍሮአልና፥

26 በደንዳና አንገቱና በወፍራሙ ጋሻው እየገሠገሠ ወደ እርሱ ይመጣበታልና፥

27 በስብም ፊቱን ከድኖአልና፥ በውፍረትም ወገቡ ተሸፍኗልና፥

28 በተደመሰሱም ከተሞች ውስጥ፥ ሰውም በሌለባቸው፥ ክምር ለመሆን በተመደቡ ቤቶች ውስጥ ተቀምጦአልና

29 ባለ ጠጋ አይሆንም፥ ሀብቱም አይጸናም፥ ጥላውንም በምድር ላይ አይጥልም፥

30 ከጨለማ አይወጣም፥ ነበልባሉም ቅርንጫፎቹን ያደርቃቸዋል፥ አበባዎቹም ይረግፋሉ።

31 ራሱን እያሳተ በከንቱ ነገር አይታመን ዋጋው ከንቱ ነገር ይሆናልና።

32 ቀኑ ሳይደርስ ጊዜው ይፈጸማል፥ ቅርንጫፉም አይለመልምም።

33 እንደ ወይን ያልበሰለውን ዘለላ ያረግፋል፥ እንደ ወይራ አበባውን ይጥላል።

34 የአምላክ አልባ ሰው ጉባኤ ፍሬ የለውም፥ የጉቦ ድንኳኖችንም እሳት ትበላለች።

35 ጉዳትን ይፀንሳሉ፥ በደልንም ይወልዳሉ፥ ሆዳቸውም ተንኰልን ያዘጋጃል።”

Síguenos en:



Anuncios


¡Síguenos en WhatsApp! Síguenos