2 ዜና መዋዕል 4 - መጽሐፍ ቅዱስ - (ካቶሊካዊ እትም - ኤማሁስ)በቤተ መቅደስ ውስጥ ያሉ ዕቃዎች 1 ንጉሥ ሰሎሞንም ርዝመቱ ሀያ ክንድ፥ ወርዱም ሀያ ክንድ፥ ቁመቱም ዐሥር ክንድ የነበረውን የናሱን መሠዊያ ሠራ። 2 ከቀለጠም ናስ ከዳር እስከ ዳር ዐሥር ክንድ፥ ቁመቱም አምስት ክንድ፥ ዙሪያውም ሠላሳ ክንድ የሆነ ክብ ኩሬ ሠራ። 3 በበታቹም ለአንድ ክንድ ዐሥር፥ ለአንድም ክንድ ዐሥር፥ እንደ በሬዎች ያሉ ቅርጾች በኩረው ላይ አዞረበት፤ ኩሬውንም በቀለጠ ጊዜ የበሬዎቹም ቅርጾች በሁለት ተራ ከእርሱ ጋር አብረው ቀልጠው ነበር። 4 በዓሥራ ሁለትም በሬዎችም ምስል ላይ ተቀምጦ ነበር፤ ከእነርሱም ሦስቱ ወደ ሰሜን ሦስቱም ወደ ምዕራብ ሦስቱም ወደ ደቡብ ሦስቱም ወደ ምሥራቅ ይመለከቱ ነበር፤ ኩሬውም በእነርሱ ላይ ተቀምጦ ነበረ፥ የሁሉም ጀርባቸው በስተ ውስጥ ነበረ። 5 ውፍረቱም አንድ ጋት ያህል ነበረ፤ ከንፈሩም እንደ ጽዋ ከንፈር፥ እንደ ሱፍ አበባ ሆኖ ተሠርቶ ነበር፤ ሦስት ሺህም የባዶስ መሥፈሪያ ይይዝ ነበር። 6 እንዲሁም ንጉሡ ዐሥር የመታጠቢያ ሳሕኖች ሠራ፥ ለሚቃጠለውም መሥዋዕት የሚቀርበውን ነገር ሁሉ እንዲያጥቡበት አምስቱን በቀኝ፥ አምስቱንም በግራ አኖራቸው፤ ኩሬው ግን ካህናት ይታጠቡበት ነበር። 7 አሥሩንም መቅረዞች እንደ ሥርዓታቸው ከወርቅ ሠርቶ አምስቱን በቀኝ አምስቱንም በግራ በመቅደሱ ውስጥ አኖራቸው። 8 አሥሩንም ገበታዎች ሠርቶ አምስቱን በቀኝ አምስቱን በግራ በመቅደስ ውስጥ አኖራቸው። አንድ መቶም የወርቅ ድስቶች ሠራ። 9 እንዲሁም የካህናቱን አደባባይ፥ ታላቁንም አደባባይ፥ የአደባባዩንም ደጆች ሠራ፥ ደጆቻቸውንም በናስ ለበጠ። 10 ኩሬውንም በቤቱ ቀኝ በደቡብ ምሥራቅ በኩል አኖረው። 11 ኪራምም ምንቸቶቹንና መጫሪያዎቹን ድስቶቹንም ሠራ። ኪራምም ለንጉሡ ለሰሎሞን በጌታ ቤት የሚሠራውን ሥራ ሁሉ ጨረሰ። 12 ሁለቱን ዓምዶች፥ ጽዋዎቹንም፥ በዓምዶቹም ላይ የነበሩትን ሁለት ጉልላቶች፥ በዓምዶቹም ላይ የነበሩትን የጉልላቶች ሁለቱን ጽዋዎች የሚሸፍኑትን ሁለቱን መርበቦች ሠራ። 13 በዓምዶቹም ላይ የነበሩትን ሁለቱን ጉልላቶች እንዲሸፍኑ፥ ለእያንዳንዱ መረበብ በሁለት በሁለት ረድፍ ያሉ ሮማኖች፥ ለሁለቱ መርበቦች አራት መቶ ሮማኖች አደረገ። 14 መቀመጫዎቹንና በመቀመጫዎቹ ላይ የሚቀመጡትን የመታጠቢያ ሳሕኖች ሠራ፤ 15 እንዲሁም አንዱንም ኩሬ፥ በበታቹም የሚሆኑትን ዐሥራ ሁለት በሬዎች አበጀ። 16 ምንቸቶቹንም መጫሪያዎቹንም ሜንጦዎቹንም ዕቃቸውንም ሁሉ ኪራም-አቢ ለንጉሡ ለሰሎሞን ለጌታ ቤት ከተሰነገለ ናስ ሠራ። 17 ንጉሡም በዮርዳኖስ ሜዳ በሱኮትና በጽሬዳ መካከል ባለው በሸክላው መሬት ላይ አስፈሰሰው። 18 ሰሎሞንም እነዚህን ዕቃዎች ሁሉ እጅግ አብዝቶ ሠራ፤ የናሱም መጠን በቍጥር አይታወቅም ነበር። 19 ሰሎሞንም በጌታ ቤት የነበረውን ዕቃ ሁሉ፥ የወርቁንም መሠዊያ፥ የተቀደሰውንም ኅብስት የሚቀመጥባቸውን ገበታዎች ሠራ፤ 20 እንዲሁም በቅድስተ ቅዱሳንም ፊት እንደ ሥርዓታቸው እንዲያበሩ መቅረዞችንና ቀንዲሎቻቸውን ከንጹሕ ወርቅ አበጀ። 21 አበባዎቹንና ቀንዲሎቹን መኮስተሪያዎቹንም ከንጹሕ ወርቅ ሠራ። 22 ጉጠቶቹንም ድስቶቹንም ሙዳዮቹንም ጀሞዎቹንም ከንጹሕ ወርቅ ሠራ። የውስጠኛውም ቤት የቅድስተ ቅዱሳን ደጆች የቤተ መቅደሱም ደጆች የወርቅ ነበሩ። |