Biblia Todo Logo
La Biblia Online
- Anuncios -


2 ዜና መዋዕል 28 - መጽሐፍ ቅዱስ - (ካቶሊካዊ እትም - ኤማሁስ)


አካዝ መንገሡ

1 አካዝ መንገሥ በጀመረ ጊዜ የሃያ ዓመት ጎልማሳ ነበረ፥ በኢየሩሳሌምም ዐሥራ ስድስት ዓመት ነገሠ፤ እንደ አባቱም እንደ ዳዊት በጌታ ፊት ቅን ነገር አላደረገም።

2 ነገር ግን በእስራኤል ነገሥታት መንገድ ሄደ፥ ደግሞም ለበኣሊም ቀልጠው የተሠሩትን ምስሎችን ሠራ።

3 ደግሞም በሄኖም ልጅ ሸለቆ ውስጥ ዐጠነ፤ ጌታ ከእስራኤል ልጆች ፊት እንዳሳደዳቸው እንደ አሕዛብም ክፉ ልማድ ልጆቹን በእሳት አቃጠለ።

4 በኮረብታው መስገጃዎችና በተራሮች ላይ በለመለመውም ዛፍ ሁሉ በታች ይሠዋና ያጥን ነበር።


ሶርያ እስራኤልን ድል መነንሣቱ

5 ስለዚህ ጌታ አምላኩ በሶርያ ንጉሥ እጅ አሳልፎ ሰጠው፤ ሶሪያውያንም ድል አደረጉት፥ ከእርሱም ብዙ ምርኮኞች ወስደው ወደ ደማስቆ አመጡ። ደግሞም በእስራኤል ንጉሥ እጅ አሳልፎ ሰጠው፤ እርሱም በታላቅ ውግያ ድል አደረገው።

6 የአባቶቻቸውንም አምላክ ጌታን ትተው ነበርና የሮሜልዩ ልጅ ፋቁሔ በአንድ ቀን ከይሁዳ መቶ ሃያ ሺህ ገደለ፤ ሁሉም ጽኑዓን ነበሩ።

7 ከኤፍሬም ወገን የነበረው ኃያል ሰው ዝክሪ የንጉሡን ልጅ መዕሤያንና የቤቱን አዛዥ ዓዝሪቃምን፥ ለንጉሡም በማዕረግ ሁለተኛ የሆነውን ሕልቃናን ገደለ።


የዖዴድ ጣልቃ ገብነት

8 የእስራኤል ልጆች ከወንድሞቻቸው ሁለት መቶ ሺህ ሴቶችን፥ ወንዶችና ሴቶች ልጆችንም ማረኩ፥ ብዙም ምርኮ ከእነርሱ ወስደው ወደ ሰማርያ አገቡ።

9 በዚያም ዖዴድ የተባለ የጌታ ነቢይ ነበረ፤ ወደ ሰማርያም የሚመጣውን ጭፍራ ሊገናኘው ወጣ፥ እንዲህም አላቸው፦ “እነሆ፥ የአባቶቻችሁ አምላክ ጌታ ይሁዳን ስለ ተቈጣ በእጃችሁ አሳልፎ ሰጣቸው፥ እናንተም ወደ ሰማይ በሚደርስ ቁጣ ገደላችኋቸው።

10 አሁንም የይሁዳና የኢየሩሳሌም ልጆች ባርያዎች ሆነው እንዲገዙላችሁ ታስባላችሁ፤ ነገር ግን አምላካችሁን ጌታን የበደላችሁት በደል በእናንተ ዘንድ የለምን?

11 አሁንም ስሙኝ፤ የጌታ ቁጣ በላያችሁ ነድዶአልና ከወንድሞቻችሁ የወሰዳችኋቸውን ምርኮኞች መልሱ።”

12 ደግሞም ከኤፍሬም ልጆች አለቆች የዮሐናን ልጅ ዓዛርያስ፥ የምሺሌሞትም ልጅ በራክያ፥ የሰሎምም ልጅ ይሒዝቅያ፥ የሐድላይም ልጅ ዓሜሳይ ከጦርነት በተመለሱት ላይ ተቃወሙአቸው።

13 እነርሱም እንዲህ አሉአቸው፦ “በጌታ ፊት በእኛ ላይ በደል ታመጡብናላችሁና፥ ኃጢአታችንንና በደላችንን ታበዙብናላችሁና የተማረኩትን ወደዚህ አታግቡ፤ በደላችን ታላቅ ነውና፥ የመቅሰፍቱም ቁጣ በእስራኤል ላይ ነውና።”

14 ተዋጊዎቹም ምርኮኞቹንና ምርኮውን በአለቆችና በጉባኤው ሁሉ ፊት ተው።

15 በስማቸውም የተጻፉ ሰዎች ተነሥተው ምርኮኞቹን ወሰዱ፥ በመካከላቸውም ራቁታቸውን ለነበሩት ሁሉ ከምርኮው አለበሱአቸው፥ አጎናጸፉአቸውም፥ ጫማም በእግራቸው አደረጉላቸው፥ መገቡአቸውም፥ አጠጡአቸውም፥ ቀቡአቸውም፤ ደካሞቹንም ሁሉ በአህዮች ላይ አስቀመጡአቸው፥ ዘንባባም ወዳለበት ከተማ ወደ ኢያሪኮ ወደ ወንድሞቻቸው አመጡአቸው፤ ወደ ሰማሪያም ተመለሱ።


አሦር ይሁዳን ለመርዳት እምቢ ማለትዋ

16 በዚያን ጊዜም ንጉሡ አካዝ እርዳታ ፈልጎ ወደ አሦር ንጉሥ ላከ፤

17 የኤዶምያስ ሰዎች ዳግመኛ መጥተው፥ ይሁዳንም መትተው ብዙ ምርኮኛ ወስደው ነበርና።

18 ደግሞም ፍልስጤማውያን በቈላውና በደቡብ በኩል ባሉት በይሁዳ ከተሞች አደጋ ጥለው ነበር፤ ቤትሳሚስንና ኤሎንን፥ ግዴሮትንም፥ ሦኮንና መንደሮችዋን፥ ተምናንና መንደሮችዋን፥ ጊምዞንና መንደሮችዋን ወስደው በዚያ ተቀምጠው ነበር።

19 የይሁዳም ንጉሥ አካዝ ጌታን ክዷልና፥ ከእርሱም እጅግ ርቋልና ጌታ ስለ እርሱ ይሁዳን አዋረደው።

20 የአሦርም ንጉሥ ቴልጌልቴልፌልሶር መጥቶ አስጨነቀው እንጂ አልረዳውም።

21 አካዝም ከጌታ ቤት ከንጉሡና ከአለቆቹም ቤት እኩሌታውን ገፈፈ፥ ለአሦርም ንጉሥ ሰጠ፤ ነገር ግን እንዲህ ማድረጉ አንዳች አልጠቀመውም።


የአካዝ መክዳትና መሞት

22 ይህም ንጉሥ አካዝ በተጨነቀ ጊዜ ጌታን መበደል አበዛ።

23 ድል ለነሡትም ለደማስቆ አማልክት፦ “የሶሪያን ነገሥታት አማልክት ረድተዋቸዋልና እኔን እንዲረዱኝ እሠዋላቸዋለሁ” ብሎ ሠዋላቸው። ነገር ግን ለእርሱና ለእስራኤል ሁሉ እንቅፋት ሆኑ።

24 አካዝም የጌታን ቤት ዕቃዎች ሁሉ ወስዶ ሰባበራቸው፥ የጌታንም ቤት ደጅ ቈለፈ፤ በኢየሩሳሌምም ማዕዘን ሁሉ መሠዊያ ሠራ።

25 በይሁዳም ከተሞች ሁሉ ለሌሎች አማልክት ለማጠን የኮረብታ መስገጃዎች አሠራ የአባቶቹንም አምላክ ጌታን አስቈጣ።

26 የቀረውም ነገርና ሥራው ሁሉ፥ የፊተኛውና የኋለኛው፥ እነሆ፥ በይሁዳና በእስራኤል ነገሥታት መጽሐፍ ተጽፎአል።

27 አካዝም ከአባቶቹ ጋር አንቀላፋ፥ በከተማይቱም በኢየሩሳሌም ቀበሩት፤ ነገር ግን ወደ እስራኤል ነገሥታት መቃብር አላገቡትም፤ ልጁም ሕዝቅያስ በእርሱ ፋንታ ነገሠ።

Síguenos en:



Anuncios


¡Síguenos en WhatsApp! Síguenos