Biblia Todo Logo
La Biblia Online
- Anuncios -


2 ዜና መዋዕል 21 - መጽሐፍ ቅዱስ - (ካቶሊካዊ እትም - ኤማሁስ)


ኢዮራም መንገሡ

1 ኢዮሣፍጥም ከአባቶቹ ጋር አንቀላፋ፥ በዳዊትም ከተማ ከአባቶቹ ጋር ተቀበረ፤ ልጁም ኢዮራም በእርሱ ፋንታ ነገሠ።

2 ለእርሱም የኢዮሣፍጥ ልጆች ዓዛርያስ፥ ይሒኤል፥ ዘካርያስ፥ ዔዛርያስ፥ ሚካኤል፥ ሰፋጥያስ የሚባሉ ወንድሞች ነበሩት፤ እነዚህ ሁሉ የይሁዳ ንጉሥ የኢዮሣፍጥ ልጆች ነበሩ።

3 አባታቸውም ብዙ ስጦታ፥ ብርና ወርቅ፥ የከበረም ዕቃ፥ በይሁዳም የተመሸጉትን ከተሞች ሰጣቸው፤ መንግሥቱን ግን የበኩር ልጁ ስለ ሆነ ለኢዮራም ሰጠ።

4 ኢዮራምም በአባቱ መንግሥት ላይ ሥልጣን ይዞ በጸና ጊዜ ወንድሞቹን ሁሉ ሌሎችንም የእስራኤልን መሳፍንት በሰይፍ ገደለ።

5 ኢዮራምም መንገሥ በጀመረ ጊዜ የሠላሳ ሁለት ዓመት ጎልማሳ ነበረ፥ በኢየሩሳሌምም ስምንት ዓመት ነገሠ።

6 የአክአብንም ልጅ አግብቶ ነበርና የአክዓብ ቤት እንዳደረገው እንዲሁ በእስራኤል ነገሥታት መንገድ ሄደ፤ በጌታም ዘንድ ክፉ የሆነውን ነገር አደረገ።

7 ነገር ግን ከዳዊት ጋር ስላደረገው ቃል ኪዳን፥ ለእርሱና ለልጆቹም በዘመናት ሁሉ መብራት ለመስጠት ስላደረገው ተስፋ፥ ጌታ የዳዊትን ቤት ለማጥፋት አልፈለገም።


ኤዶምያስ ማመፁ

8 በእርሱም ዘመን ኤዶምያስ በይሁዳ ላይ ዓመፀ፥ ለራሱም ንጉሥ አነገሠ።

9 ኢዮራምም ከአለቆቹና ከሰረገሎቹ ሁሉ ጋር ተሻገረ፤ በሌሊትም ተነሥቶ እርሱንና የሰረገሎቹን አለቆች ከብበው የነበሩትን የኤዶምያስን ሰዎች መታ።

10 ኤዶምያስ ግን በይሁዳ ላይ እስከ ዛሬ ድረስ ዓመፀ፥ በዚያንም ዘመን ልብና ደግሞ በእርሱ ላይ ዓመፀ፥ የአባቶቹን አምላክ ጌታን ትቶ ነበርና።


የነቢዩ ኤልያስ ደብዳቤ

11 ዳግምም በይሁዳ ተራሮች ላይ በከፍታ ላይ የሚገኙ የማምለኪያ ሥፍራዎችን ሠራ፥ በኢየሩሳሌምም የተቀመጡትን እንዲያመነዝሩ አደረጋቸው፥ ይሁዳንም አሳተው።

12 ከነቢዩም ከኤልያስ እንዲህ የሚል ደብዳቤ መጣለት፦ “የአባትህ የዳዊት አምላክ ጌታ እንዲህ ይላል፦ ‘በአባትህ በኢዮሣፍጥ መንገድ በይሁዳም ንጉሥ በአሳ መንገድ አልሄድህምና፥

13 በእስራኤል ነገሥታት መንገድ ግን ሄደሃልና፥ የአክዓብም ቤት እንዳደረገ ይሁዳንና በኢየሩሳሌም የሚኖሩትን እንዲያመነዝሩ አድርገሃልና፥ ከአንተም የሚሻሉትን የአባትህን ቤት ወንድሞችህን ገድለሃልና፥

14 እነሆ፥ ጌታ ሕዝብህንና ልጆችህን ሚስቶችህንም ያለህንም ሁሉ በታላቅ መቅሰፍት ይቀስፋል።

15 አንተም ከደዌው ጽናት የተነሣ አንጀትህ በየዕለቱ እስኪ ወጣ ድረስ በክፉ የአንጀት ደዌ ትያዛለህ።’ ”

16 ጌታም የፍልስጥኤማውያንና በኢትዮጵያውያን አጠገብ የሚኖሩትን የዓረባውያንን የቊጣ መንፈስ በኢዮራም ላይ አስነሣ።

17 ወደ ይሁዳም ወጡ፥ ወረርዋትም፥ የንጉሡንም ቤት ዕቃ ሁሉ፥ ወንዶች ልጆቹንም ሴቶች ልጆቹንም ማረኩ፤ ከታናሹም ልጅ ከአካዝያስ በቀር ልጅ አላስቀሩለትም።


ኢዮራም መታመሙና መሞቱ

18 ከዚህም ሁሉ በኋላ ጌታ በማይፈወስ ደዌ አንጀቱን ቀሰፈው።

19 ከቀንም ወደ ቀን እንዲህ ሆነ፤ ከሁለት ዓመት በኋላ ከደዌው ጽናት የተነሣ አንጀቱ ወጣ፥ በክፉም ደዌ ሞተ። ሕዝቡም ለአባቶቹ ያደርገው እንደ ነበረ ለእርሱ የመቃብር ወግ አላደረገም።

20 መንገሥም በጀመረ ጊዜ የሠላሳ ሁለት ዓመት ጎልማሳ ነበረ፥ በኢየሩሳሌምም ስምንት ዓመት ነገሠ፤ ማንም ሳያዝንለት ከዚህ ዓለም በሞት ተሰናበተ፤ በዳዊትም ከተማ እንጂ በነገሥታቱ መቃብር አልቀበሩትም።

Síguenos en:



Anuncios


¡Síguenos en WhatsApp! Síguenos