ይህ መፅሐፍ በእግዚአብሔር አልተነፀረም እና የክርስቲያን ካኖን ወይም የአይሁድ ታናክ ክፍል አይደለም። ለታሪክና ለጥናት ዓላማ ብቻ ይታያል። ሙሉ ማብራሪያን ይመልከቱ መጽሐፈ ሲራክ 11 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)1 ድሃ በጥበቡ ይከብራል፤ በመኳንንትም መካከል ይቀመጣል። 2 ስለ መልከ መልካምነቱ ለሰው አታድላ፤ ስለ መልከ ጥፉነቱም ሰውን አትናቀው። 3 ንብ ከወፎች ሁሉ ታንሳለች፤ ማርዋ ግን ከሁሉ ይጣፍጣል። 4 በልብስህ ጌጥ አትታበይ። በከበርህበትም ወራት ራስህን አታኵራ። የእግዚአብሔር ሥራው ልዩ፥ ጥበቡም ከሰው የተሰወረ ነውና። 5 በምድር የወደቁ መኳንንት ብዙ ናቸው፤ ዘውድ የተቀዳጀ ባሕታዊም አለ። 6 ፈጽመው የተዋረዱ መኳንንት ብዙ ናቸው፤ በሌሎችም እጅ የወደቁ መኳንንት ብዙ ናቸው። 7 ሳትመረምር አትንቀፍ፤ አስቀድመህ ተረዳ፥ በኋላም ትቈጣለህ። 8 ሳትሰማ አትመልስ፤ በሌላውም ነገር ውስጥ አትግባ። 9 ግዳጅህም ባልሆነ ነገር አትጨነቅ፤ ከኀጢአተኞች ጋርም በፍርድ አትቀመጥ። 10 ልጄ ሆይ፥ ሥራህን አታብዛ፤ ብታበዛ ትከብር ዘንድ አያሠለጥንህምና፤ ብትሮጥ አታመልጥም፥ ብትከተልም አታገኝም። 11 የሚቸኩልና የሚሠራ፥ የሚደክምም አለ፤ ነገር ግን እጅግ ይቸገራል። 12 ደክሞ ሳለም የማይለምን፥ ምንም ማድረግ ሳይችል የሚገዛ አለ፤ ምንም ቢጸና ፈጽሞ የሚቸገር አለ። 13 እግዚአብሔር ግን በመልካም ዐይን ቢያየው ከችግሩ ያነሣዋል። ከፍ ከፍ ያደርገዋል፥ ያከብረዋል፥ ብዙ ሰዎችም ያደንቁታል። 14 መልካምና ክፉ፥ ሕይወትና ሞት፤ ድህነትና ብልጽግና ከእግዚአብሔር ዘንድ ናቸው። 15 ጥበብ፥ ማስተዋልና ሕግን ማወቅ፥ ፍቅርና መልካም ሥራን መሥራት ከእግዚአብሔር ዘንድ ይመጣሉ። 16 ስሕተትና ጨለማ ከመወለዳቸው ጀምሮ ከኃጥኣን ጋር ኖረዋል። ክፋትም በእርሱ ደስ ከሚሰኙት ጋር አብሮ ያድጋል። 17 የእግዚአብሔር ጸጋው ጻድቃንን ትጠብቃቸዋለች፤ ፈቃዱም ለዘለዓለም ደስ ታሰኛለች። 18 እየነፈገ በንፍገቱ ብዛት የሚከብር ሰው አለ። በእርስዋም ደስታውን ይፈጽምባታል። 19 ያርፍ ዘንድ ተስፋ ባደረገ ጊዜ፥ “እበላለሁ እጠጣለሁ፥ እንግዲህስ ደስ ይለኛል፥ በቃኝም” ባለ ጊዜ፥ የሚሞትባትን ቀን አያውቅም፤ ገንዘቡንም ሁሉ ለባዕድ ትቶ እርሱ ይሞታል። 20 በቃል ኪዳንህ ቁም፤ በእርሱም ተማር፤ በሥራህም ሸምግል። 21 የኀጢአተኞች ሥራቸው አያስጐምጅህ፥ በእግዚአብሔር እመን፥ ድካምህንም ተስፋ አድርግ፥ ሁሉ በአንድ ጊዜ በእግዚአብሔር ዘንድ ቀሊል ነውና፥ ድሃውንም ድንገት ያከብረዋልና። 22 የእግዚአብሔር በረከት ለጻድቃን ዋጋቸው ናት፥ የጻድቅም በረከቱ ትበዛለች። 23 “የአገልግሎቴ ትርፍ ምንድን ነው? ከእንግዲህስ ወዲያ የማገኘው መልካም ነገር ምንድን ነው?” አትበል። 24 “እንግዲህስ በቃኝ፥ ከእንግዲህም ወዲያ አልቸገርም” አትበል። 25 በመልካም ቀን ጊዜ ክፉ ይረሳል፤ በክፉ ቀንም ጊዜ መልካም ይረሳል። 26 የሞት ቀን በእግዚአብሔር ዘንድ ቀሊል ነው፤ ለሰው እንደ ሥራው ዋጋውን ይከፍለዋልና። 27 በክፉ ቀን ጥጋብ ያቀናጣል፤ የሰውም ሥራው በፍጻሜ ዘመኑ ይታወቃል። 28 ፍጻሜውን ሳታይ ሰውን ብፁዕ አትበለው፥ የሰው አኗኗሩ በልጆቹ ይገለጣል። ጓደኛን ስለ መምረጥ 29 ተንኰለኛ ብዙ ይተነኰልብሃልና ያገኘኸውን ሰው ሁሉ ወደ ቤትህ አታግባ። 30 ቆቅ በወጥመድ ይያዛል፥ የትዕቢተኛ ሰውም ልቡ እንደዚሁ ነው፤ መከራውንም እንደ ጕበኛ ይመለከታታል። 31 ተንኰለኛ ሰው በበጎ ፋንታ ክፉ ነገርን ይከፍልሃል፤ ሳይኖርብህ ነውርን ያወጣብሃል። 32 በእሳት ትንታግ ብዛት ፍሙ ይበዛል፤ ኀጢአተኛ ሰውም ሰውነቱን ያድድናታል። 33 ክፉ ነገርን ይሠራብሃልና፥ ሁልጊዜ ስድብን እንዳያደርግብህ ከክፉ ሰው ተጠበቅ። 34 ባዕድ ሰውን ከአንተ ጋር ብታሳድር ያውክሃል፤ ይወነጅልሃል፥ ከገንዘብህም ይለይሃል። |