ሉቃስ 14 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)ሆዱ የተነፋውን ሰው እንደ ፈወሰ 1 ከዚህም በኋላ ሄዶ ከፈሪሳውያን አለቆች ወደ አንዱ ቤት በሰንበት ቀን እህል ሊበላ ገባ፤ እነርሱ ግን ይጠባበቁት ነበር። 2 እነሆም፥ ሆዱ የተነፋ አንድ ሰው በፊቱ ነበር። 3 ጌታችን ኢየሱስም መልሶ ሕግ ዐዋቂዎችንና ፈሪሳውያንን፥ “በሰንበት ድውይ መፈወስ ይገባልን? ወይስ አይገባም?” ብሎ ጠየቃቸው። 4 እነርሱም ዝም አሉ፤ ይዞም ፈወሰውና ሰደደው። 5 “ከእናንተ በሬው ወይም አህያው በጕድጓድ ውስጥ የወደቀበት አንድ ሰው ቢኖር ዕለቱን በሰንበት ቀን ያነሣው የለምን?” አላቸው። 6 ስለዚህም ነገር ሊመልሱለት አልተቻላቸውም። በራስጌ መቀመጥን ስለሚወዱ ሰዎች 7 በምሳ ላይ ለነበሩትም ወደ ላይኛው ወንበር ሲሽቀዳደሙ ባያቸው ጊዜ ምሳሌ መስሎ አስተማራቸው። 8 እንዲህም አለ፥ “ለምሳ የጠራህ ሰው ቢኖርና ብትሄድ በላይኛው መቀመጫ አትቀመጥ፤ ምናልባት ከአንተ የሚበልጥ ይመጣ ይሆናል። 9 በኋላ ያ አንተንም እርሱንም የጠራ መጥቶ፦ ይህን ቦታ ለእርሱ ተውለት ይልሃልና፤ ያንጊዜም አፍረህ ትመለሳለህ፤ ወደ ዝቅተኛ ቦታም ትወርዳለህ። 10 የጠራህ ሰው ቢኖርና ብትሄድ ግን የጠራህ በመጣ ጊዜ ወዳጄ ወደ ላይኛው መቀመጫ ውጣ ይልህ ዘንድ በታችኛው መቀመጫ ተቀመጥ፤ ያንጊዜም ከአንተ ጋር ለማዕድ በተቀመጡት ሰዎች ፊት ክብር ይሆንልሃል። 11 ራሱን ከፍ የሚያደርግ ሁሉ ይዋረዳልና፤ ራሱንም ያሚያዋርድ ከፍ ይላልና።” 12 የጠራውንም እንዲህ አለው፥ “በበዓል ምሳ ወይም ራት በምታደርግበት ጊዜ ወዳጆችህንና ወንድሞችህን፥ ዘመዶችህንና ጎረቤቶችህን፥ ባለጸጎች ባልንጀሮችህንም አትጥራ፤ እነርሱም ይጠሩሃልና፤ ብድርም ይሆንብሃልና። 13 ነገር ግን በበዓል ምሳ በምታደርግበት ጊዜ ድሆችንና ጦም አዳሪዎችን፥ ዕውሮችን፥ እጅና እግርም የሌላቸውን ጥራ። 14 አንተም ብፁዕ ትሆናለህ፤ የሚከፍሉህ የላቸውምና፤ ነገር ግን ጻድቃን በሚነሡበት ጊዜ ዋጋህን ታገኛለህ።” 15 ለምሳ ከተቀመጡትም አንዱ ይህን ሰምቶ፥ “በእግዚአብሔር መንግሥት እህል የሚበላ ብፁዕ ነው” አለው። ለምሳ ስለ መጠራት 16 ጌታችን ኢየሱስም እንዲህ አላቸው፥ “አንድ ሰው ታላቅ ምሳ አደረገና ብዙ ሰዎችን ጠራ። 17 ለምሳ የተጠሩበትም ቀን በደረሰ ጊዜ የታደሙትን ይጠራቸው ዘንድ አገልጋዩን ላከ፤ እርሱም ሄዶ የታደሙትን፦ አሁን ምሳውን ፈጽመን አዘጋጅተናልና ኑ አላቸው። 18 ሁሉም በአንድ ቃል ተባብረው እንቢ አሉ፤ የመጀመሪያው፦ እርሻ ገዝችአለሁ፤ ሄጄም ላያት እሻለሁ፤ እንቢ እንደ አላልሁ ቍጠርልኝ በለው አለው። 19 ሁለተኛውም፦ አምስት ጥማድ በሬ ገዝቻለሁ፤ ላያቸውና ልፈትናቸው እሄዳለሁ፤ እንደ መጣሁ፥ እንቢ እንደ አላልሁም ቍጠርልኝ በለው አለው። 20 ሦስተኛውም፦ ሚስት አግብችአለሁ፤ ስለዚህ ልመጣ አልችልም በለው አለው። 21 አገልጋዩም ተመልሶ ለጌታው ይህንኑ ነገረው፤ ያንጊዜም ባለቤቱ ተቈጣ፤ አገልጋዩንም፦ ፈጥነህ ወደ አደባባይና ወደ ከተማው ጐዳና ሂድ፤ ድሆችንና ጦም አዳሪዎችን፥ ዕውሮችንና አንካሶችን ወደዚህ አምጣልኝ አለው። 22 ከዚህም በኋላ አገልጋዩ፦ አቤቱ እንደ አዘዝኸኝ አደረግሁ፤ ገናም ቦታ አለ አለው። 23 ጌታውም አገልጋዩን፦ ወደ መንገዶችና ወደ ከተማው ቅጥር ፈጥነህ ሂድና ቤቴ እንዲመላ ይገቡ ዘንድ ግድ በላቸው አለው። 24 ከእነዚህ ከታደሙት ሰዎች አንዱ ስንኳን ማዕዴን እንደማይቀምሳት እነግራችኋለሁ።” ጌታን ስለ መከተል 25 ከዚህም በኋላ ብዙ ሰዎች አብረውት ሲሄዱ መለስ ብሎ እንዲህ አላቸው። 26 “ወደ እኔ የሚመጣ፥ ሊከተለኝም የሚወድ አባቱንና እናቱን፥ ሚስቱንና ልጆቹን፥ ወንድሞቹንና እኅቶቹን፥ የራሱንም ሰውነት እንኳ ቢሆን የማይጠላ ደቀ መዝሙሬ ሊሆን አይችልም። 27 መስቀሉን ተሸክሞ ሊከተለኝ የማይመጣ ደቀ መዝሙሬ ሊሆን አይችልም።” ቤት ስለሚሠራው ሰው ምሳሌ 28 “ከእናንተም ወገን የግንብ ቤት መሥራት የሚወድ ቢኖር ይጨርሰው ዘንድ የሚችል እንደ ሆነ አስቀድሞ ተቀምጦ የሚፈጅበትን የማያስብ ማን ነው? 29 መሠረቱን ጥሎ መጨረስ ያቃተውም እንደ ሆነ ያዩት ሁሉ፥ 30 ‘ይህ ሰው ሊሠራ ጀመረ፤ ግን መጨረስ ተሳነው’ እያሉ ሊዘብቱበት ይጀምራሉ። 31 ንጉሥም ሌላውን ንጉሥ ይወጋ ዘንድ ሊሄድ ቢወድ ሁለት እልፍ ይዞ ወደ እርሱ የሚመጣውን በአንድ እልፍ ሊዋጋው ይችል እንደ ሆነ አስቀድሞ ተቀምጦ ይመክር የለምን? 32 ያለዚያ ግን፥ ገና በሩቁ ሳለ አማላጆች መልእክተኞችን ልኮ ዕርቅ ይለምናል። 33 እንግዲህ እንደዚሁ ከእናንተ ወገን ከሁሉ ያልወጣ፥ የእርሱ ገንዘብ ከሆነውም ሁሉ ያልተለየ ደቀ መዝሙሬ ሊሆን አይችልም። 34 “ጨው መልካም ነው፤ ጨው አልጫ ከሆነ እንግዲህ በምን ያጣፍጡታል? 35 ለምድርም ቢሆን፥ ለፍግ መቆለያም ቢሆን አይረባም፤ ነገር ግን ወደ ውጭ ይጥሉታል፤ የሚሰማ ጆሮ ያለው ይስማ።” |