Biblia Todo Logo
የመስመር ላይ መጽሐፍ ቅዱስ

- ማስታወቂያዎች -

ይህ መፅሐፍ በእግዚአብሔር አልተነፀረም እና የክርስቲያን ካኖን ወይም የአይሁድ ታናክ ክፍል አይደለም። ለታሪክና ለጥናት ዓላማ ብቻ ይታያል። ሙሉ ማብራሪያን ይመልከቱ

መጽ​ሐፈ ኩፋሌ 9 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)

1 በሠ​ላሳ ሦስ​ተ​ኛ​ውም ኢዮ​ቤ​ልዩ መጀ​መ​ሪያ እን​ዲህ ሆነ፤ ለካ​ምና ለሴም ለያ​ፌ​ትም ርስት ልት​ሆ​ና​ቸው ከአ​ን​ደ​ኛው ሱባዔ በመ​ጀ​መ​ሪ​ያው ዓመት ወደ እነ​ርሱ ከተ​ላ​ክን ከእኛ አንዱ ባለ​በት ምድ​ርን ሦስት አድ​ር​ገው ከፈ​ሉ​አት፤ ልጆ​ቹ​ንም ጠራ፤ እነ​ር​ሱና ልጆ​ቻ​ቸ​ውም ወደ እርሱ ቀረቡ፤ ሦስቱ ልጆ​ቹም የሚ​ይ​ዙ​ትን ምድር በዕጣ ከፈለ።

2 እጃ​ቸ​ው​ንም ዘር​ግ​ተው ከአ​ባ​ታ​ቸው ከኖኅ እጅ መጽ​ሐ​ፉን ተቀ​በሉ። ርስት አድ​ርጎ የሚ​ይ​ዘው የሴም ዕጣም ለል​ጆ​ቹና ለልጅ ልጆቹ ለዘ​ለ​ዓ​ለም በመ​ጽ​ሐፍ የም​ድር መካ​ከል ወጣ። ከአ​ር​በ​ኞች ተራራ መካ​ከል ከው​ኃ​ውም መውጫ ጀምሮ እስከ ጢና ወንዝ ድረስ ወጣ።

3 ክፍ​ሉም በዚህ ወንዝ መካ​ከል ወዳለ ወደ ምዕ​ራብ ይደ​ር​ሳል፤ ይህም ወንዝ ከእ​ር​ስዋ እስ​ከ​ሚ​ወ​ጣ​በት እስከ ጥልቁ ውኃ እስ​ኪ​ቀ​ርብ ድረስ ወደ​ዚያ ይሄ​ዳል። ውኃ​ውም ወደ ሚኦት ባሕር ይፈ​ስ​ሳል፤ ይህም ወንዝ እስከ ታላቁ ባሕር ድረስ ይሄ​ዳል፤ በደ​ቡ​ብም በኩል ያለው ሀገር ሁሉ ለያ​ፌት ደረሰ፤ በሰ​ሜን በኩል ያለ​ውም ሀገር ሁሉ ለሴም ደረሰ።

4 ወደ ኮራሶ እስ​ኪ​ቀ​ርብ ድረስ ይሄ​ዳል። ይኸ​ውም ወደ ሰሜን የሚ​መ​ለ​ከት ሕፅነ ልሳን ነው። ክፍ​ሉም ወደ ታላቁ ባሕር ይደ​ር​ሳል። ይህች ባሕር ልሳነ ባሕረ ግብፅ ትባ​ላ​ለ​ችና ወደ ሰሜን ወደ​ም​ታ​ሳይ ወደ ልሳን መግ​ቢያ እስ​ኪ​ቀ​ርብ ድረስ አቅ​ንቶ ይሄ​ዳል።

5 ከዚ​ያም ወደ ሰሜን ታዘ​ነ​ብ​ላ​ለች፤ ወደ ታላቁ ባሕር መግ​ቢያ ወደ ውኃ​ውም ዳርቻ ትደ​ር​ሳ​ለች፤ ወደ አፍ​ራም ግራ ትደ​ር​ሳ​ለች፤ ግዮን ወደ​ሚ​ባል ፈሳሽ ውኃም እስ​ክ​ት​ቀ​ርብ ድረስ ትደ​ር​ሳ​ለች፤ ወደ ግዮ​ንም ውኃ ቀርባ ወደ​ዚህ ፈሳሽ ዳርቻ ትደ​ር​ሳ​ለች።

6 ወደ ኤደን ገነት ወደ ሰሜ​ንም ቀኝ እስ​ክ​ት​ቀ​ርብ ድረስ ወደ ምሥ​ራቅ ትሄ​ዳ​ለች፤ ከኤ​ዶም ምድር ሁሉ ምሥ​ራቅ፥ ከሀ​ገ​ሩም ሁሉ ምሥ​ራቅ ወደ ምሥ​ራቅ ይመ​ለ​ሳል። ስሙ ራፋ ወደ​ሚ​ባል ተራራ ምሥ​ራቅ እስ​ኪ​ቀ​ርብ ድረስ ይመ​ጣል፤ ወደ ጢና ወንዝ መውጫ ዳር​ቻም ይወ​ር​ዳል።

7 ይህ​ችም ክፍል ለዘ​ለ​ዓ​ለም ሊይ​ዙ​አት ለሴ​ምና ለል​ጆቹ፥ ለልጅ ልጆ​ቹም እስከ ዘለ​ዓ​ለም ድረስ በዕጣ ወጣች።

8 ኖኅም ይህ ክፍል የሴ​ምና የል​ጆቹ ዕጣ ነውና ደስ አለው። “የሴም አም​ላክ እግ​ዚ​አ​ብ​ሔር ይመ​ስ​ገን፥ እግ​ዚ​አ​ብ​ሔ​ርም በሴም ማደ​ሪያ ይደር” ብሎ​አ​ልና በአፉ በት​ን​ቢት የተ​ና​ገ​ረ​ውን ነገር ሁሉ ዐሰበ። የኤ​ዶም ገነት ከከ​በሩ የከ​በ​ረች፥ የእ​ግ​ዚ​አ​ብ​ሔ​ርም ማደ​ሪያ እንደ ሆነች ዐው​ቆ​አ​ልና። ደብረ ሲና በም​ድረ በዳ መካ​ከል ናት፥ ደብረ ጽዮ​ንም በም​ድር ዕን​ብ​ርት መካ​ከል ናት፥ እነ​ዚህ ሦስቱ ሁሉ አንዱ በአ​ንዱ አን​ጻር ለቅ​ድ​ስና ተፈ​ጠሩ።

9 በአፉ ቃለ እግ​ዚ​አ​ብ​ሔ​ርን እን​ዲ​ና​ገር ያደ​ረ​ገ​ውን የአ​ማ​ል​ክት አም​ላክ እግ​ዚ​አ​ብ​ሔ​ርን እስከ ዘለ​ዓ​ለም ድረስ አመ​ሰ​ገ​ነው፤ የተ​ባ​ረከ ክፍ​ልና በረ​ከት ለሴ​ምና ለል​ጆቹ፥ ለልጅ ልጆ​ቹም እስከ ዘለ​ዓ​ለም ድረስ እንደ ደረ​ሳ​ቸው ዐወቀ።

10 የኤ​ዶም ምድር ሁሉ፥ የኤ​ር​ትራ ባሕር ዳርም ሁሉ፥ የም​ሥ​ራቅ ምድር ሁሉ በኤ​ር​ት​ራና በተ​ራ​ሮቹ በኩል ያለው ሕንድ፥ የባ​ሳን ሀገር ሁሉና የሊ​ባ​ኖ​ስም ሀገር ሁሉ፥ የካ​ፍ​ቱር ደሴ​ቶ​ችና የሳ​ኔር ተራራ ሁሉ፥ አማ​ናና የደ​ቡ​ባ​ዊው አሱር ተራራ፥ የኤ​ላም ሀገር ሁሉ፥ አሱ​ርና ባቢል፥ ሱሳ​ንም ማእ​ዳ​ይና የአ​ራ​ራት ሀገር ሁሉ፥ በደ​ቡብ በኩል ከአ​ለው ከአ​ሱር ተራራ ማዶ የባ​ሕሩ ወደብ እንደ ደረ​ሱት ዐወቀ። የተ​ባ​ረ​ከ​ችና ሰፊ የሆ​ነች፥ በው​ስ​ጥ​ዋም ያለ ሁሉ እጅግ ያማረ ምድር፤

11 ሁለ​ተ​ኛ​ውም ዕጣ ወደ ግዮን ማዶ በገ​ነት ቀኝ በሰ​ሜን በኩል ለካም ወጣ፥ ወደ ሰሜ​ንም ይደ​ር​ሳል። ዋዕይ ወደ ጸና​በት ተራ​ራም ሁሉ ይደ​ር​ሳል፤ በአ​ጤል አን​ጻር ወዳለ ወደ ምዕ​ራብ ይደ​ር​ሳል። ወደ ማዕ​ከክ ባሕር እስ​ኪ​ቀ​ርብ ድረ​ስም ወደ ምዕ​ራብ ይደ​ር​ሳል። ይህ​ች​ውም የሚ​ጠ​ፋው ሁሉ ወደ እር​ስዋ የሚ​ወ​ር​ድ​ባት ሀገር ናት። ወደ ደቡብ ወደ ጋዴት ዳርቻ ይወ​ጣል። ወደ ግዮን ወን​ዝም እስ​ኪ​ቀ​ርብ ድረስ ወደ ባሕሩ ዳርቻ ወደ ታላቁ ባሕር ይመ​ጣል።

12 ግዮን የተ​ባ​ለው ወን​ዝም በኤ​ዶም ገነት ቀኝ እስ​ኪ​ቀ​ርብ ድረስ ይሄ​ዳል። ለዘ​ለ​ዓ​ለም ለሚ​ይ​ዛት ለካ​ምና ለል​ጆቹ፥ ለወ​ገ​ና​ቸ​ውም እስከ ዘለ​ዓ​ለም ድረስ በዕጣ የወ​ጣች ሀገር ይህች ናት።

13 ለያ​ፌ​ትም ሦስ​ተ​ኛው ዕጣ ወጣ። ጢና ወደ​ሚ​ባል ወንዝ ማዶ ወደ ፈሳ​ሾች መውጫ ወደ ደቡብ ወጣ። ወደ ደቡብ ምሥ​ራቅ፥ ወደ ጎግ አው​ራ​ጃም ሁሉና ወደ ምሥ​ራ​ቃ​ቸው ሁሉ ይደ​ር​ሳል፥ ከደ​ቡ​ብም ወደ ደቡብ ይደ​ር​ሳል። ወደ ቄልጥ ተራ​ራና ወደ ደቡብ፥ ወደ ማሉ​ቅም ባሕር ይደ​ር​ሳል። እስከ ባሕሩ መውጫ ዳርቻ ድረስ ወደ ጋዴት ምሥ​ራ​ቅም ይመ​ጣል። ወደ ፋራ መግ​ቢ​ያም እስ​ኪ​ቀ​ርብ ድረስ ይሄ​ዳል። ወደ ምሥ​ራቅ ወደ ማኡታ ባሕር ወደ​ሚ​ሄ​ደው ወደ አፌ​ራ​ግም ይመ​ለ​ሳል፤ ወደ ውኃው ዳርቻ ወደ ራፋ ተራራ እስ​ኪ​ቀ​ር​ብም ድረስ ጢና ወደ​ተ​ባ​ለው ወንዝ ወደ ደቡብ ምሥ​ራቅ ይሄ​ዳል። ደቡ​ብ​ንም ይዞ​ራል።

14 ለዘ​ለ​ዓ​ለሙ በር​ስ​ት​ነት ዕጣ የሚ​ይ​ዛት፥ ለያ​ፌ​ትና ለል​ጆቹ፥ ለወ​ገ​ኖ​ቹም የወ​ጣ​ች​ለት ምድር ይህች ናት። ታላ​ላቅ ደሴ​ቶ​ች​ዋም አም​ስት ናቸው። በደ​ቡብ በኩል ያለ​ች​ውም ሀገር ሰፊ ናት። ነገር ግን የያ​ፌት ሀገር ቀዝ​ቃዛ ናት፤ የካ​ምም ሀገር በረሃ ናት፤ የሴም ሀገር ግን ከው​ር​ጭና ከዋ​ዕይ ጋር የተ​ቀ​ላ​ቀ​ለች ናትና ቆላም ደጋም አይ​ደ​ለ​ችም።

15 ካም በል​ጆቹ መካ​ከል አካ​ፈለ። የመ​ጀ​መ​ሪ​ያው ዕጣም ለኩሽ ወደ ምሥ​ራቅ ወጣ፥ ምዕ​ራቡ ለም​ጽ​ራ​ይም ወጣ፥ ምዕ​ራ​ቡም ለፉጥ ወጣ፤ ምዕ​ራ​ቡም ለከ​ነ​ዓን ወጣ፤ በም​ዕ​ራ​ቡም በኩል ባሕር ነበር።

16 ሴምም በል​ጆቹ መካ​ከል አካ​ፈለ። መጀ​መ​ሪ​ያው ዕጣ ለኤ​ላ​ምና ለል​ጆቹ እስከ ሕን​ደኬ ምድር ሁሉ ምሥ​ራቅ እስ​ኪ​ቀ​ርብ ድረስ ወደ ጤግ​ሮስ ወንዝ ምሥ​ራቅ ወጣ፤ ኤር​ት​ራም በእጁ ነበር። የዲ​ዳን ውኃ፥ የሞ​ብሪ ተራ​ሮች፥ የኤላ ሀገር ሁሉ፥ የሱ​ሳም ሀገር ሁሉ፥ በፊ​ር​ኖክ በኩል ያለው ሁሉ፥ እስከ ኤር​ትራ ባሕ​ርና እስከ ጢና ወንዝ።

17 ለአ​ሶ​ርም ሁለ​ተ​ኛው ዕጣ ወጣ፤ የአ​ሱ​ርና ነነዌ ሀገር ሁሉ፥ ሰና​ዖ​ርም፥ ሳድም እስከ ሕን​ደኬ አቅ​ራ​ቢያ ድረስ። ወደ ወድፋ ፈሳ​ሽም ይደ​ር​ሳል።

18 ለአ​ር​ፋ​ክ​ስ​ድም ሦስ​ተ​ኛው ዕጣ ወጣ። የከ​ላ​ው​ዴ​ዎን አው​ራጃ ሀገር ሁሉ፥ ለኤ​ር​ትራ ባሕር የቀ​ረ​በው የኤ​ፍ​ራ​ጥስ ምሥ​ራ​ቅም፥ ወደ ግብፅ እስ​ከ​ም​ት​መ​ለ​ከ​ተው እስከ ልሳነ ባሕር አቅ​ራ​ቢያ ድረስ የም​ድረ በዳው ውኃ ሁሉ፥ የሊ​ባ​ኖ​ስና የሳ​ኔር ሀገር፥ አማ​ናም፥ እስከ ኤፍ​ራ​ጥስ ድረስ።

19 ለአ​ራ​ምም አራ​ተ​ኛው ዕጣ ወጣ፤ በጤ​ግ​ሮ​ስና በኤ​ፍ​ራ​ጥስ መካ​ከል የመ​ስ​ጴ​ጦ​ምያ ሀገር ሁሉ በከ​ላ​ው​ዴ​ዎን ደቡብ ወዳለ እስከ አሱር አቅ​ራ​ቢያ ድረስ፥ የአ​ራ​ራ​ትም ሀገር ሁሉ የእ​ርሱ ነው።

20 ለሉ​ድም አም​ስ​ተ​ኛው ዕጣ ወጣ፤ የአ​ሱር ተራራ ሁሉ፥ ወደ ታላቁ ባሕር እስ​ኪ​ቀ​ርብ ድረስ የእ​ርሱ ዕጣ ነው። ወደ ወን​ድሙ ወደ አሶር ምሥ​ራ​ቅም ይደ​ር​ሳል።

21 ያፌ​ትም ምድረ ርስ​ትን በል​ጆቹ መካ​ከል ከፈለ። መጀ​መ​ሪ​ያ​ውም ዕጣ ከደ​ቡብ አን​ጻር ጀምሮ እስከ ጢና ወንዝ ድረስ በም​ሥ​ራቅ በኩል ለሴ​ሜር ወጣ። በደ​ቡ​ብም በኩል የደ​ቡብ ዙሪያ ሁሉ ለሚ​አት ባሕር እስ​ኪ​ቀ​ርብ ድረስ ለማ​ጎግ ወጣ።

22 ከም​ዕ​ራቡ ጀምሮ እስከ ደሴ​ቶ​ችና እስከ ደሴ​ቶ​ችም ዳርቻ ድረስ ለሁ​ለቱ ወን​ድ​ሞቹ ሁሉ ይይዝ ዘንድ ለማ​ዳይ ደረሰ።

23 ለኢ​ዮ​እ​ያ​ንም አራ​ተ​ኛው ዕጣ ወጣ፥ ደሴቱ ሁሉ፥ በሉ​ድም አን​ጻር ያሉ ደሴ​ቶች ሁሉ።

24 ለቶ​ቤ​ልም እስከ ሁለ​ተ​ኛ​ዪቱ ልሳን ድረስ ወደ ሉድ ዕጣ በም​ት​ቀ​ርብ በል​ሳን መካ​ከል አም​ስ​ተ​ኛው ዕጣ ወጣ። የሁ​ለ​ተ​ኛ​ዪ​ቱም ልሳን አው​ራጃ እስከ ሦስ​ተ​ኛ​ዪቱ ልሳን ድረስ ነው።

25 ለሞ​ሳ​ክም ስድ​ስ​ተ​ኛው ዕጣ ወጣ። እስከ ጋዴር ምሥ​ራ​ቅም እስ​ኪ​ቀ​ርብ ድረስ የሦ​ስ​ተ​ኛ​ዪቱ ልሳን አው​ራጃ ሁሉ።

26 ለቲ​ራ​ስም ሰባ​ተ​ኛው ዕጣ ወጣ። በባ​ሕር መካ​ከል ያሉ፥ ለካም ዕጣ የሚ​ቀ​ርቡ ታላ​ላቁ አራቱ ደሴ​ቶች፤ የክ​ማ​ቱሪ ደሴ​ቶ​ችም በር​ስ​ት​ነት ዕጣ ለአ​ር​ፋ​ክ​ስድ ልጆች ወጡ፤ የኖ​ኅም ልጆች ለል​ጆ​ቻ​ቸው በአ​ባ​ታ​ቸው በኖኅ ፊት እን​ዲህ አድ​ር​ገው ከፈሉ። በዕ​ጣው ያል​ወ​ጣ​ለ​ትን ክፍል ይይዝ ዘንድ የሚ​ፈ​ል​ገ​ውን እያ​ን​ዳ​ን​ዱን አምሎ ረገመ።

27 ሁሉም ይሁን አሉ። ስለ​ሚ​ያ​ጸ​ይፍ ክፉ ኀጢ​አ​ታ​ቸው ሁሉ፥ ምድ​ር​ንም በበ​ደ​ልና በር​ኵ​ሰት፥ በዝ​ሙ​ትና በኀ​ጢ​አ​ትም ስለ ሞሉ​አት እግ​ዚ​አ​ብ​ሔር አም​ላክ በሰ​ይ​ፍና በእ​ሳት ይፈ​ር​ድ​ባ​ቸው ዘንድ እስከ ፍርድ ቀን ድረስ በራ​ሳ​ቸ​ውና በል​ጆ​ቻ​ቸው፥ በዘ​ራ​ቸ​ውም እስከ ዘለ​ዓ​ለም ይሁን አሉ።

ተከተሉን:



ማስታወቂያዎች