Biblia Todo Logo
የመስመር ላይ መጽሐፍ ቅዱስ

- ማስታወቂያዎች -

ይህ መፅሐፍ በእግዚአብሔር አልተነፀረም እና የክርስቲያን ካኖን ወይም የአይሁድ ታናክ ክፍል አይደለም። ለታሪክና ለጥናት ዓላማ ብቻ ይታያል። ሙሉ ማብራሪያን ይመልከቱ

መጽ​ሐፈ ኩፋሌ 10 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)

1 በዚህ ኢዮ​ቤ​ልዩ በሦ​ስ​ተ​ኛው ሱባዔ ርኩ​ሳን አጋ​ን​ንት የኖ​ኅን የልጅ ልጆች ያስ​ቱ​አ​ቸ​ውና አእ​ም​ሮ​አ​ቸ​ውን እያ​ሳጡ ያጠ​ፉ​አ​ቸው ጀመሩ።

2 የኖ​ኅም ልጆች ወደ አባ​ታ​ቸው ወደ ኖኅ መጡ። የልጅ ልጆ​ቹ​ንም የሚ​ያ​ስ​ቱና የሚ​ያ​ደ​ነ​ቁሩ፥ የሚ​ገ​ድ​ሉም የአ​ጋ​ን​ን​ትን ነገር ነገ​ሩት።

3 ኖኅም ወደ ፈጣ​ሪው ወደ እግ​ዚ​አ​ብ​ሔር እን​ዲህ ሲል ጸለየ፥ “ምሕ​ረ​ት​ህን አድ​ር​ገህ ያዳ​ን​ኸኝ፥ ልጆ​ች​ንም ከጥ​ፋት ውኃ ያዳ​ን​ኻ​ቸው፥ የጥ​ፋ​ትን ልጅ እን​ዳ​ጠ​ፋ​ኸው እን​ድ​ጠፋ ያላ​ደ​ረ​ግ​ኸኝ፥ በእኔ ላይ ያለ ይቅ​ር​ታህ ብዙ ነውና፥ ቸር​ነ​ት​ህም በሰ​ው​ነቴ በዝ​ታ​ለ​ችና፥ በሥጋ ውስጥ ሁሉ ያሉ የነ​ፍ​ሳት ፈጣሪ ሆይ፥ ይቅ​ር​ታህ በል​ጆች ላይ ከፍ ከፍ ይበል፤ ክፉ​ዎች አጋ​ን​ን​ትም ከዚህ ዓለም እን​ዳ​ያ​ጠ​ፉ​አ​ቸው በላ​ያ​ቸው አይ​ሠ​ል​ጥኑ።

4 አን​ተም እኔን ባር​ከኝ። የብዙ ብዙ እን​ሆን ዘንድ፥ ምድ​ር​ንም እን​ሞ​ላት ዘንድ፥ ልጆ​ችን ባር​ካ​ቸው። አን​ተም በሕ​ይ​ወት ያሉ የእ​ነ​ዚህ ረቂ​ቃን አጋ​ን​ንት አባ​ቶ​ቻ​ቸው ትጉ​ሃን ያደ​ረ​ጉ​ትን ታው​ቃ​ለህ። ይዘህ በፍ​ርድ ቦታ አግ​ዛ​ቸው፤ እነ​ርሱ ክፉ​ዎች ናቸ​ውና፥ ለማ​ጥ​ፋ​ትም ተፈ​ጥ​ረ​ዋ​ልና አም​ላኬ ሆይ፥ የእ​ኔን የባ​ሪ​ያ​ህን ልጆች አያ​ጥፉ፤ በሕ​ይ​ወት በሚ​ኖሩ ሰዎች ነፍ​ስም አይ​ሠ​ል​ጥኑ፥ አንተ ብቻ ፍር​ዳ​ቸ​ውን ታው​ቃ​ለ​ህና ከዛሬ ጀምሮ እስከ ዘለ​ዓ​ለም ድረስ በጻ​ድ​ቃን ልጆች ላይ አይ​ሠ​ል​ጥኑ።”

5 አም​ላ​ካ​ች​ንም ሁሉን አስ​ረን እና​ግዝ ዘንድ አዘ​ዘን። የአ​ጋ​ን​ን​ትም አለቃ መስ​ቴማ መጥቶ፥ “አቤቱ ፈጣ​ሪዬ፥ ከእ​ነ​ርሱ በፊቴ ጥቂት አስ​ቀ​ር​ልኝ፤ ቃሌ​ንም ይስሙ፤ እኔ የማ​ዝ​ዛ​ቸ​ው​ንም ሁሉ ያድ​ርጉ፤ ከእ​ነ​ርሱ ካል​ቀ​ሩ​ልኝ በሰው ልጆች ላይ የፈ​ቃ​ዴን ሥል​ጣን ማድ​ረግ አል​ች​ል​ምና። የሰው ልጆች ክፋ​ታ​ቸው ብዙ ስለ ሆነ ከፍ​ርዴ አስ​ቀ​ድሞ እነ​ርሱ ለማ​ጥ​ፋ​ትና ለማ​ሳት ናቸ​ውና።”

6 “በፊቱ ዐሥ​ረ​ኛው ነገድ ይቅሩ፤ ዘጠ​ኙን ነገድ ግን ወደ ፍርድ ቦታ ያው​ር​ዱ​አ​ቸው” አለ። እር​ሱም በቀና ሥራ ጸን​ተው የሚ​ኖሩ እን​ዳ​ይ​ደሉ፥ በእ​ው​ነ​ትም የሚ​ጣሉ እን​ዳ​ይ​ደሉ ያው​ቃ​ልና የሚ​ድ​ኑ​በ​ትን ሁሉ ለኖኅ እና​ስ​ተ​ም​ረው ዘንድ ከእኛ አን​ዱን አዘ​ዘው።

7 እኛም እንደ ቃሉ አደ​ረ​ግን፤ ፈጽ​መው የከፉ አጋ​ን​ን​ትን በፍ​ርድ ቦታ አስ​ረን አጋ​ዝን። ዐሥ​ረ​ኛ​ውን ነገድ ግን በሰ​ይ​ጣን ፊት በም​ድር ይገዙ ዘንድ አስ​ቀ​ረን። በም​ድር እን​ጨ​ቶ​ችም ያድን ዘንድ የደ​ዌ​ያ​ቸ​ውን መድ​ኀ​ኒት ከማ​ሳ​ታ​ቸው ጋር ለኖኅ ነገ​ር​ነው።

8 ኖኅም በየ​መ​ድ​ኀ​ኒቱ ዓይ​ነት ሁሉ እን​ዳ​ስ​ተ​ማ​ር​ነው በመ​ጽ​ሐፍ ሁሉን ጻፈ። ክፉ​ዎች አጋ​ን​ን​ትም የኖ​ኅን ልጆች እን​ዳ​ይ​ከ​ታ​ተሉ ተጋዙ።

9 ከል​ጆቹ ሁሉ ይልቅ ፈጽሞ እር​ሱን ይወ​ደው ነበ​ርና የጻ​ፋ​ቸ​ውን መጻ​ሕ​ፍት ሁሉ ለታ​ላቁ ልጁ ለሴም ሰጠው። ኖኅም እንደ አባ​ቶቹ ሞተ፤ አራ​ራት በሚ​ባ​ልም ሀገር በሉ​ባር ተቀ​በረ፤ ኖኅም በሕ​ይ​ወቱ ዘጠኝ መቶ አምሳ ዓመት ጨረሰ። ይህም ዐሥራ ዘጠኝ ኢዮ​ቤ​ልዩ ሁለት ሱባ​ዔና አም​ስት ዓመት ነው። ፍጹም በሆ​ነ​ባት ሥራው በም​ድር የኖ​ረው ሕይ​ወቱ ከሄ​ኖክ በቀር ከሰው ልጆች ይልቅ የከ​በረ ነበር። የሄ​ኖክ ሥራ በፍ​ርድ ቀን የት​ው​ል​ዱን ሁሉ ሥራ ይነ​ግር ዘንድ ለዘ​ለ​ዓ​ለም ትው​ልድ ምስ​ክር ሊሆን ተፈ​ጥ​ሮ​አ​ልና።

10 በሠ​ላሳ ሦስ​ተ​ኛው ኢዮ​ቤ​ልዩ ከሁ​ለ​ተ​ኛው ሱባዔ በመ​ጀ​መ​ሪ​ያው ዓመት ፋሌክ ስምዋ ሎምና የሚ​ባል ሚስ​ትን አገባ፤ ይህ​ች​ውም የሴ​ና​ዖር ልጅ ናት። በዚ​ሁም ሱባዔ በአ​ራ​ተ​ኛው ዓመት ወንድ ልጅን ወለ​ደ​ች​ለት። ከአ​ራ​ራት ምድር ወደ ምሥ​ራቅ ወደ ሰና​ዖር ሀገር ስለ ተሰ​ደዱ በሰ​ና​ዖር ሀገር ከተ​ማ​ንና አም​ባን ይሠሩ ዘንድ የሰው ልጆች በጽኑ ምክር እነሆ፥ ክፉ​ዎ​ችን ሆኑ ብሎ​አ​ልና ስሙን ራግው አለው። ወደ ሰማይ እን​ወ​ጣ​በ​ታ​ለን ሲሉ በዘ​መኑ ከተ​ማ​ንና ግን​ብን ሠር​ተ​ዋ​ልና፤ መሥ​ራ​ትም ጀም​ረ​ዋ​ልና።

11 በአ​ራ​ተ​ኛ​ውም ሱባዔ ጡቡን ሠር​ተው በእ​ሳት ተኰሱ። ጡቡም እንደ ድን​ጋይ ሆነ​ላ​ቸው፤ የሚ​መ​ር​ጉ​በት ጭቃ​ውም ከባ​ሕ​ርና በሰ​ና​ዖር ሀገር ከው​ኃ​ዎች ምንጭ የሚ​ወጣ የባ​ሕ​ርን አረፋ ሆነ​ላ​ቸው።

12 በአ​ርባ ሦስት ዓመ​ትም ሠሩት። እየ​ሠ​ሩም ነበሩ። ወር​ዱም ሁለት መቶ ሦስት ጡብ ነበር፤ የጡ​ቡም ከፍታ የር​ዝ​መቱ አንድ ሦስ​ተኛ ነበር። ቁመቱ አም​ስት ሺህ አራት መቶ ሠላሳ ሦስት ክንድ ከሁ​ለት ስን​ዝር ወደ ላይ ወጣ። አቆ​ል​ቋ​ዩም ዐሥራ ሦስት ምዕ​ራፍ ነበር።

13 አም​ላ​ካ​ችን እግ​ዚ​አ​ብ​ሔ​ርም እኛን እን​ዲህ አለን፥ “እነሆ፥ አንድ ቋንቋ የሆነ ሕዝብ ግንብ ይሠራ ጀመር፤ አሁ​ንም ከእ​ነ​ርሱ ፈጽ​መን እን​ዳ​ና​ጠፋ ኑ እን​ው​ረድ፤ የአ​ን​ዱ​ንም ቋንቋ አንዱ እን​ዳ​ይ​ሰማ፥ ቋን​ቋ​ቸ​ውን እን​ደ​ባ​ል​ቀው፤ በየ​ከ​ተ​ማ​ውና በየ​አ​ሕ​ዛቡ ይበ​ተኑ፤ ከዚህ በኋ​ላም እስከ ፍርድ ቀን ድረስ አን​ዲት ምክር በላ​ያ​ቸው አት​ኑር።”

14 እግ​ዚ​አ​ብ​ሔ​ርም ወረደ፤ እኛም የሰው ልጆች የሠ​ሩ​ትን ከተ​ማ​ው​ንና ግን​ቡን እናይ ዘንድ ከእ​ርሱ ጋር ወረ​ድን፤ ቋን​ቋ​ቸ​ው​ንም ደባ​ለቀ፤ አን​ዱም የአ​ን​ዱን ነገር አል​ሰ​ማም። ከዚ​ያም በኋላ ከተ​ማ​ው​ንና ግን​ቡን መሥ​ራት ተዉ።

15 ስለ​ዚ​ህም አም​ላክ በዚያ የሰው ልጆ​ችን ቋንቋ ሁሉ ደባ​ል​ቆ​አ​ልና የሰ​ና​ዖር ሀገር ሁሉ ባቢል ተባ​ለች፤ ከዚ​ያም በየ​ከ​ተ​ማ​ቸ​ውና በየ​ቋ​ን​ቋ​ቸው፥ በየ​ወ​ገ​ና​ቸ​ውም ተበ​ተኑ።

16 እግ​ዚ​አ​ብ​ሔ​ርም ታላቅ ነፋ​ስን አም​ጥቶ ግን​ባ​ቸ​ውን በም​ድር ላይ ገለ​በጠ፤ እነሆ፥ እር​ሱም በሰ​ና​ዖር ሀገር በአ​ሦ​ርና በባ​ቢ​ሎን መካ​ከል ነው። ስም​ዋ​ንም ድቀት አላት። በሠ​ላሳ አራ​ተ​ኛ​ውም ኢዮ​ቤ​ልዩ በአ​ራ​ተ​ኛው ሱባዔ በአ​ን​ደ​ኛው ዓመት መጀ​መ​ሪያ ከሰ​ና​ዖር ሀገር ተበ​ተኑ።

17 ካምና ልጆ​ቹም ለእ​ርሱ ወደ ተያ​ዘች በደ​ቡብ ሀገር በዕጣ ወዳ​ገ​ኛት ሀገር ሄዱ። ከነ​ዓ​ንም እስከ ግብፅ ውኃ መፍ​ሰሻ ድረስ ያለ​ች​ውን የሊ​ባ​ኖ​ስን ሀገር እጅግ ያማ​ረች እንደ ሆነች አየ። ወደ ርስ​ቱም ሀገር ወደ ባሕሩ መግ​ቢያ አል​ሄ​ደም፤ እር​ሱም ከም​ሥ​ራቅ ጀምሮ እስከ ምዕ​ራብ በሊ​ባ​ኖ​ስና በባ​ህሩ ዙሪያ ምድር ኖረ።

18 አባቱ ካምና ወን​ድ​ሞቹ ኩሳ፥ ሚጽ​ራ​ይ​ምም፥ “የአ​ንተ ዕጣ ባል​ሆ​ነች ሀገር ኖረ​ሃ​ልና፥ በዕ​ጣም አል​ወ​ጣ​ች​ል​ን​ምና እን​ዲህ አታ​ድ​ርግ አሉት። እን​ደ​ዚህ ብታ​ደ​ርግ አን​ተና ልጆ​ችህ በዚህ ምድር ትጠ​ፋ​ላ​ችሁ፤ በክ​ር​ክ​ርም ኖራ​ች​ኋ​ልና በክ​ር​ክር የተ​ረ​ገ​ማ​ችሁ ትሆ​ና​ላ​ችሁ፤ ልጆ​ች​ህም በጠብ ይጠ​ፋሉ፤ አን​ተም ለዘ​ለ​ዓ​ለም ትጠ​ፋ​ለህ።

19 ለሴ​ምና ለል​ጆቹ በዕ​ጣ​ቸው ወጥ​ቶ​አ​ልና በሴም ሀገር አት​ኑር፤ አን​ተም የተ​ረ​ገ​ምህ ነህ። በአ​ባ​ታ​ችን በኖ​ኅና በቅ​ዱሱ ፈራጅ ፊት ለመ​ር​ገም በመ​ሐላ ከተ​ዘ​ጋ​ጀን ከኖኅ ልጆች ሁሉ ተለ​ይ​ተህ አንተ የተ​ረ​ገ​ምህ ትሆ​ና​ለህ” አሉት። እርሱ ግን አል​ሰ​ማ​ቸ​ውም፤ ከኤ​ማት ጀምሮ እስከ ግብፅ መግ​ቢያ ድረስ በሊ​ባ​ኖስ ሀገር ኖረ፤ ልጆ​ቹም እስ​ከ​ዚህ ቀን ድረስ በዚያ ኖሩ። ስለ​ዚህ ያች ሀገር የከ​ነ​ዓን ሀገር ተባ​ለች።

20 ያፌ​ትና ልጆቹ ግን ወደ ባሕር ሄዱ፤ ድር​ሻ​ቸው በሆነ ሀገ​ርም ኖሩ።

21 ማዳ​ይም ባሕር ያለ​ባ​ትን ሀገር አየ፤ ነገር ግን በፊቱ ደስ አላ​ሰ​ኘ​ች​ውም፤ የሚ​ስቱ ወን​ድ​ሞች ከሆኑ ከኤ​ላ​ምና ከአ​ሱር፥ ከአ​ር​ፋ​ክ​ስ​ድም ለምኖ እስ​ከ​ዚ​ህች ቀን ድረስ የሚ​ስቱ ወን​ድ​ሞች አቅ​ራ​ቢያ በሚ​ሆን በሜ​ቄ​ዶን ሀገር ኖረ። የእ​ር​ሱን ቦታና የል​ጆ​ቹን ቦታ ሜቄ​ዶ​ን​ንም በአ​ባ​ታ​ቸው በማ​ዳይ ስም ጠራው።

22 በሠ​ላሳ አም​ስ​ተ​ኛ​ውም ኢዮ​ቤ​ልዩ በሦ​ስ​ተ​ኛው ሱባዔ በመ​ጀ​መ​ሪ​ያው ዓመት ራግው ስምዋ ዑራ የም​ት​ባል ሚስ​ትን አገባ፤ ይህ​ች​ውም የኬ​ሴድ ልጅ የዑር ልጅ ናት። ወንድ ልጅ​ንም ወለ​ደ​ች​ለት፤ ስሙ​ንም ሴሩግ ብሎ ጠራው።

23 በዚህ ኢዮ​ቤ​ልዩ በሰ​ባ​ተ​ኛው ሱባዔ የኖኅ ልጆች ሰውን ለመ​ማ​ረ​ክና ለመ​ግ​ደል፥ እያ​ን​ዳ​ን​ዱም ወን​ድ​ሙን ለመ​ግ​ደል፥ የሰ​ው​ንም ደም በም​ድር ላይ ለማ​ፍ​ሰስ፥ ደም​ንም ለመ​ብ​ላት፥ የጸኑ ከተ​ማ​ዎ​ች​ንና አን​ባ​ዎ​ችን፥ ግን​ቦ​ች​ንም ለመ​ሥ​ራት ሕዝብ በሕ​ዝብ ላይ ለመ​ነ​ሣት፥ በመ​ን​ግ​ሥ​ትም ላይ አስ​ቀ​ድሞ ለመ​ሾም፥ ሕዝቡ በሕ​ዝቡ ፊት፥ አሕ​ዛ​ቡም በአ​ሕ​ዛቡ ፊት ወደ ሰልፍ ለመ​ሄድ፥ ከተ​ማም ከከ​ተማ ጋር ለመ​ጣ​ላት፥ ሁሉም ክፉ ሥራ ለመ​ሥ​ራት፥ የጦር መሣ​ሪ​ያ​ንም ለመ​ግ​ዛት፥ ለል​ጆ​ቻ​ቸ​ውም ሰል​ፍን ለማ​ስ​ተ​ማር መዋ​ጋት ጀመሩ። አንዱ አገር ሌላ​ውን አገር ይማ​ርክ፥ ሴት ባሪ​ያ​ንና ወንድ ባሪ​ያ​ንም ይገዙ ጀመር።

24 የኬ​ሴድ ልጅ ዑርም በከ​ላ​ው​ዴ​ዎን ያለች የዑ​ርን ከተማ ሠራ፤ ስም​ዋ​ንም በእ​ርሱ ስምና በአ​ባቱ ስም ጠራ። ጣዖ​ቶ​ች​ንም ሠሩ፤ እያ​ን​ዳ​ን​ዱም ለራሱ ቀርፆ ለሠ​ራው ጣዖት ይሰ​ግድ ነበር፤ ጣዖ​ት​ንና ምስ​ልን፥ ርኵ​ሰ​ት​ንም ይሠሩ ጀመር፤ ክፉ​ዎች አጋ​ን​ን​ትም ኀጢ​አ​ት​ንና ርኵ​ሰ​ትን ይሠሩ ዘንድ ይረ​ዱና ያስቱ ነበር።

25 አለ​ቃው መስ​ቴ​ማም ይህን ሁሉ ለመ​ሥ​ራት ይበ​ረታ ነበር፤ ኀጢ​አ​ት​ንና በደ​ልን ሁሉ፥ ፈጽ​ሞም ለማ​ጥ​ፋ​ትና ክህ​ደ​ትን ሁሉ ለማ​ሠ​ራት፥ በም​ድ​ርም ደምን ለማ​ፍ​ሰስ ከእጁ በታች ያሉ የአ​ጋ​ን​ን​ትን እጅ ይልክ ነበር።

26 ስለ​ዚ​ህም ሰው ሁሉ በደ​ል​ንና ኀጢ​አ​ትን ሁሉ ወደ መሥ​ራት ተመ​ል​ሶ​አ​ልና፥ የሴ​ሩሕ ስም ሴሩግ ተባለ። እር​ሱም አደገ፤ ለሚ​ስ​ቱም እናት አባት አቅ​ራ​ቢያ በሆነ በከ​ላ​ው​ዴ​ዎን ዕጣ በዑር ኖረ። ጣዖ​ት​ንም ያመ​ልክ ነበር፤ እር​ሱም በሠ​ላሳ ሰባ​ተ​ኛው ኢዮ​ቤ​ልዩ በአ​ም​ስ​ተ​ኛው ሱባዔ በመ​ጀ​መ​ሪ​ያው ዓመት ሚስ​ትን አገባ፤ ስም​ዋም ሜልካ ይባ​ላል፤ ይህ​ች​ውም የአ​ባቱ የእ​ኅት ልጅ የካ​ቤር ልጅ ናት፥ በዚህ ሱባዔ በመ​ጀ​መ​ሪ​ያው ዓመት ናኮ​ርን ወለ​ደ​ች​ለት።

27 እር​ሱም አደገ፤ በከ​ላ​ው​ዴ​ዎን ዕጣ በዑ​ርም ኖረ። አባ​ቱም በሰ​ማይ ምል​ክት ለማ​ም​ዋ​ረ​ትና ለመ​ጠ​ን​ቆል የከ​ዋ​ክ​ብ​ትን ምር​ምር አስ​ተ​ማ​ረው።

28 በሠ​ላሳ ሰባ​ተ​ኛው ኢዮ​ቤ​ልዩ በስ​ድ​ስ​ተ​ኛው ሱባዔ በመ​ጀ​መ​ሪ​ያው ዓመት ሚስ​ትን አገባ፤ ስም​ዋም ኢዮ​ስካ ይባ​ላል። ይህ​ችም የከ​ለ​ዳ​ው​ያን ወገን የኔ​ስ​ቴግ ልጅ ናት። በዚህ ሱባዔ በሰ​ባ​ተ​ኛው ዓመት ታራ የሚ​ባል ወንድ ልጅን ወለ​ደ​ች​ለት።

29 አለ​ቃው መስ​ቴ​ማም ምድ​ርን ለማ​ጥ​ፋት፥ በም​ድር ላይ የተ​ዘ​ራ​ውን ዘር ይበሉ ዘንድ ወፎ​ች​ንና ቁራ​ዎ​ችን ሰደደ። ቁራ​ዎ​ችም ሳያ​ርሱ የሰው ልጆች አዝ​መ​ራን ይቀሙ ዘንድ ከም​ድር ላይ ዘሩን ይለ​ቅሙ ጀመር። ስለ​ዚ​ህም አሞ​ራ​ዎ​ችና ወፎች ያስ​ቸ​ግ​ሩ​አ​ቸው ነበ​ርና፥ ዘራ​ቸ​ው​ንም ይበ​ሉ​ባ​ቸው ነበ​ርና ስሙን ታራ አለው።

30 ከወ​ፎ​ቹም ፊት የተ​ነሣ ዓመ​ቶች ድርቅ ይሆኑ ጀመር፤ የእ​ን​ጨ​ቱ​ንም ፍሬ ሁሉ ከዛ​ፎቹ ላይ እየ​ለ​ቀሙ ይበሉ ነበር፥ በዘ​መ​ና​ቸው ከም​ድር ፍሬ ሁሉ ጥቂት ማዳን ቢች​ሉም በታ​ላቅ ኀይል ነበር። በሠ​ላሳ ዘጠ​ነ​ኛ​ውም ኢዮ​ቤ​ልዩ በሁ​ለ​ተ​ኛው ሱባዔ በመ​ጀ​መ​ሪ​ያው ዓመት ታራ ሚስት አገባ፤ ስም​ዋም ኤድና ይባ​ላል፤ ይህ​ች​ውም የአ​ባቱ የእ​ኅት ልጅ የም​ት​ሆን የአ​ብ​ራም ልጅ ናት። በዚ​ህም ሱባዔ በሰ​ባ​ተ​ኛው ዓመት ወንድ ልጅን ወለ​ደ​ች​ለት። የልጁ ልጅ ሳይ​ፀ​ነስ ሙቶ​አ​ልና ስሙን በእ​ናቱ አባት ስም አብ​ራም አለው።

31 ያም ልጅ ሰው ሁሉ ጣዖ​ታ​ቱን በመ​ከ​ተ​ልና ኀጢ​አ​ትን በመ​ሥ​ራት እን​ደ​ሚ​ስት የም​ድ​ርን ስሕ​ተት ያውቅ ጀመር።

32 አባ​ቱም መጽ​ሐ​ፍን አስ​ተ​ማ​ረው፤ የሁ​ለት ሱባዔ ዓመት ልጅም ነበረ። ከእ​ር​ሱም ጋር ለጣ​ዖት እን​ዳ​ይ​ሰ​ግድ አባ​ቱን ከመ​ከ​ተል ተለየ።

33 ከሰ​ዎች ልጆች ስሕ​ተ​ትም ያድ​ነው ዘንድ፥ ዕጣ​ውም ርኵ​ሰ​ት​ንና ፌዝን በመ​ከ​ተል ወደ ስሕ​ተት እን​ዳ​ይ​ሆን ሁሉን ወደ ፈጠረ ወደ እግ​ዚ​አ​ብ​ሔር ይጸ​ልይ ጀመር።

34 በም​ድ​ርም ዘርን ለመ​ዝ​ራት ጊዜው ደረሰ፤ ዘራ​ቸ​ው​ንም ከአ​ሞ​ራ​ዎች ይጠ​ብቁ ዘንድ ሁሉም በአ​ን​ድ​ነት ወጡ።

35 አብ​ራ​ምም ከወጡ ልጆች ጋር ወጣ። እር​ሱም የዐ​ሥራ አራት ዓመት ልጅ ነበረ፤ ብዙ​ዎች ቁራ​ዎ​ችም ዘርን ይለ​ቅሙ ዘንድ መጡ። አብ​ራ​ምም በም​ድር ላይ ሳያ​ርፉ በፊ​ታ​ቸው ይሮጥ ነበር፤ ዘር​ንም ለመ​ል​ቀም በም​ድር ላይ ሳያ​ርፉ፥ “ወደ መጣ​ች​ሁ​በት ቦታ ተመ​ለሱ እንጂ ወደ ምድር አት​ው​ረዱ” እያለ ይጮኽ ነበር፤ እነ​ር​ሱም ተመ​ለሱ።

36 በዚ​ያ​ችም ቀን ብዙ​ዎች ቁራ​ዎ​ችን ለመ​ከ​ላ​ከል ሰው አስ​ቀ​መጡ። አብ​ራ​ምም ባለ​በት በዚያ እርሻ ሁሉ ከቁ​ራ​ዎች ሁሉ አን​ድም ቁራ አላ​ረ​ፈም።

37 በእ​ር​ሻ​ዎቹ ውስጥ ከእ​ርሱ ጋር ያሉት ሰዎች ሁሉ ሲጮ​ኽና አሞ​ራ​ዎ​ችን ሁሉ፦ ተመ​ለሱ ሲላ​ቸው ይሰ​ሙት ነበር፤ ስሙም በከ​ላ​ው​ዴ​ዎን ምድር ሁሉ ከፍ ከፍ አለ።

38 የሚ​ዘ​ሩም ሰዎች ሁሉ በዚህ ዓመት ወደ እርሱ ይመጡ ነበር። የዘሩ ወራ​ትም እስ​ኪ​ፈ​ጸም ድረስ ከእ​ነ​ርሱ ጋር ይሄድ ነበር። ምድ​ራ​ቸ​ው​ንም ዘሩ፤ በዚ​ያም ዓመት የሚ​በቃ እህ​ልን አገቡ፤ በል​ተ​ውም ጠገቡ።

39 አብ​ራ​ምም በአ​ም​ስ​ተ​ኛው ሱባዔ በአ​ን​ደ​ኛው ዓመት የበሬ ዕቃ ለሚ​ሠ​ሩት ሰዎች እን​ጨት መጥ​ረ​ብን አስ​ተ​ማረ።

40 በም​ድ​ርም ላይ የበሬ ዕቃ ሠሩ፤ በላ​ዩም ዘርን ያኖር ዘንድ በድ​ግሩ አን​ጻር እር​ፍን ሠራ፤ ዘሩም በእ​ርፉ ጫፍ ወርዶ በም​ድር ይሸ​ፈን ነበር። ከዚ​ህም በኋላ ከአ​ሞ​ራ​ዎቹ ፊት የተ​ነሣ አል​ፈ​ሩም ነበር፤ በእ​ር​ፉም ድግር ሁሉ ላይ እን​ዲህ አደ​ረጉ፤ በም​ድ​ርም ላይ የእ​ር​ፉን ድግር አኖሩ።

41 ዘር​ንም ዘሩ፤ ሰዎ​ችም ሁሉ አብ​ራም እን​ዳ​ዘ​ዛ​ቸው ሁሉን አደ​ረጉ። ከዚያ በኋላ ከአ​ሞ​ራ​ዎቹ የተ​ነሣ አል​ፈ​ሩም።

42 በስ​ድ​ስ​ተ​ኛው ሱባዔ በሰ​ባ​ተ​ኛው ዓመት አብ​ራም አባቱ ታራን፥ “አባ አባቴ፥” ብሎ ጠራው። እር​ሱም፥ “ልጄ ሆይ፥ እነ​ሆኝ፥” አለው። እር​ሱም፥ “ምንም እስ​ት​ን​ፋስ የላ​ቸ​ው​ምና አንተ ከም​ታ​መ​ል​ካ​ቸ​ውና በፊ​ታ​ቸው ከም​ት​ሰ​ግ​ድ​ላ​ቸው ከእ​ነ​ዚህ ከጣ​ዖ​ታቱ ለእኛ ምን ረድ​ኤ​ትና ደስታ አለን? ድዳ​ዎች ናቸ​ውና፥ ልቡ​ና​ንም የሚ​ያ​ስቱ ናቸ​ውና አታ​ም​ል​ኩ​አ​ቸው።

43 ሰማ​ይን የፈ​ጠረ፥ በም​ድ​ርም ላይ ዝና​ብ​ንና ጠልን የሚ​ያ​ወ​ር​ደ​ውን፥ በም​ድር ላይ ሁሉን የሚ​ያ​ደ​ር​ገ​ውን፥ ሁሉ​ንም በቃሉ የፈ​ጠ​ረ​ውን፥ ሕይ​ወ​ትም ሁሉ ከእ​ርሱ የሚ​ገ​ኘ​ውን የሰ​ማ​ይን አም​ላክ አም​ልኩ።

44 እስ​ት​ን​ፋስ የሌ​ላ​ቸው ጣዖ​ታ​ቱን እና​ንተ ለምን ታመ​ል​ካ​ላ​ችሁ? እነ​ርሱ የሰው ሥራ ናቸ​ውና፥ እና​ንተ በጫ​ን​ቃ​ችሁ ትሸ​ከ​ሙ​አ​ቸ​ዋ​ላ​ች​ሁና፥ ለሚ​ሠ​ሩ​አ​ቸው ሰዎች ታላቅ ተዋ​ርዶ ናቸው እንጂ ከእ​ነ​ርሱ ረድ​ኤት አይ​ገ​ኝ​ምና፥ ለሚ​ያ​መ​ል​ኩ​አ​ቸ​ውም ሰዎች የል​ቡና ስሕ​ተት ናቸ​ውና አታ​ም​ል​ኩ​አ​ቸው።”

45 አባ​ቱም፥ “ልጄ ሆይ፤ እኔም አው​ቃ​ለሁ፤ ነገር ግን በፊ​ታ​ቸው እን​ዳ​ገ​ለ​ግል ላደ​ረ​ጉኝ ለሕ​ዝቡ ምን አደ​ር​ጋ​ለሁ? እው​ነት ነገ​ር​ንም ብነ​ግ​ራ​ቸው፥ ያመ​ል​ኩ​አ​ቸ​ውና ያመ​ሰ​ግ​ኑ​አ​ቸው ዘንድ ልቡ​ና​ቸው እነ​ር​ሱን ተከ​ት​ላ​ለ​ችና ይገ​ድ​ሉ​ኛል፤ ልጄ ሆይ፥ እን​ዳ​ይ​ገ​ድ​ሉህ ዝም በል” አለው።

46 ለሁ​ለቱ ወን​ድ​ሞ​ቹም ይህን ነገር ነገ​ራ​ቸው፤ እነ​ር​ሱም ተቈ​ጡት፤ እር​ሱም ዝም አለ።

47 በአ​ር​ባው ኢዮ​ቤ​ልዩ በሁ​ለ​ተ​ኛው ሱባዔ በሰ​ባ​ተ​ኛው ዓመት አብ​ራም ሚስት አገባ፤ ስም​ዋም ሶራ ይባ​ላል፤ ይህ​ች​ውም የአ​ባቱ ልጅ ናት፤ ሚስ​ትም ሆነ​ችው።

48 ወን​ድሙ አራ​ንም በሦ​ስ​ተ​ኛው ሱባዔ በሦ​ስ​ተ​ኛው ዓመት ሚስት አገባ። በዚ​ህም ሱባዔ በሰ​ባ​ተ​ኛው ዓመት ልጅ ወለ​ደ​ች​ለት፤ ስሙ​ንም ሎጥ አለው። ወን​ድሙ ናኮ​ርም ሚስ​ትን አገባ።

ተከተሉን:



ማስታወቂያዎች