ይህ መፅሐፍ በእግዚአብሔር አልተነፀረም እና የክርስቲያን ካኖን ወይም የአይሁድ ታናክ ክፍል አይደለም። ለታሪክና ለጥናት ዓላማ ብቻ ይታያል። ሙሉ ማብራሪያን ይመልከቱ ትንቢተ ዳንኤል 8 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)ዳንኤል በራእይ ያያቸው አውራ በግና ፍየል 1 በመጀመሪያ ከተገለጠልኝ ራእይ በኋላ፥ ንጉሡ ብልጣሶር በነገሠ በሦስተኛው ዓመት ለእኔ ለዳንኤል ራእይ ተገለጠልኝ፤ 2 በኤላም አውራጃ በአለው በሱሳ ግንብ ሳለሁ ራእይ አየሁ፤ በኡባልም ወንዝ አጠገብ ነበርሁ። 3 ዐይኖችንም አቅንቼ አየሁ፤ እነሆም አንድ የበግ አውራ መጥቶ በኡባል አጠገብ ቆመ፤ ሁለት ቀንዶች ነበሩት፤ ቀንዶቹም ረዣዥሞች ነበሩ፤ አንዱ ቀንዱ ግን ከሌላው ቀንዱ ይበልጥ ነበር፤ ረዥሙም ቀንዱ በስተኋላ የበቀለ ነበር። 4 አውራውም በግ ወደ ምዕራብ፥ ወደ ሰሜንም፥ ወደ ደቡብም በቅንዱ ሲጐሽም አየሁ፤ አራዊትም ሁሉ በፊቱ አይቆሙም ነበር፤ ከእጁም የሚያድን አልነበረም፤ እንደ ፈቃዱም አደረገ፤ ከፍ ከፍም አለ። 5 እኔ ዳንኤልም የባሪ ክፍል በምትሆን በሱሳ ነበርሁ፤ ስመለከትም እነሆ ከምዕራብ ወገን አንድ አውራ ፍየል በምድር ሁሉ ፊት ላይ ወጣ፤ ምድርንም አልነካም፤ ለፍየሉም በዐይኖቹ መካከል አንድ ታላቅ ቀንድ ነበረው። 6 ሁለትም ቀንድ ወደ አለው፥ በኡባል ወንዝም ፊት ቆሞ ወደ አየሁት አውራ በግ መጣ፤ በኀይሉም ቍጣ ፈጥኖ ወደ እርሱ ሮጠ። 7 ወደ አውራውም በግ ቀርቦ አየሁት፤ እርሱም ዘልሎ ወጣበት፤ አውራውንም በግ መታ፤ ሁለቱንም ቀንዶች ሰበረ፤ አውራውም በግ በፊቱ ሊቆም ኀይል አልነበረውም፤ እርሱም በምድር ላይ ጥሎ ረገጠው፤ አውራውንም በግ ከእጁ ያድን ዘንድ የሚችል አልነበረም። 8 አውራውም ፍየል ራሱን እጅግ ታላቅ አደረገ፤ በበረታም ጊዜ ታላቁ ቀንዱ ተሰበረ፤ ወደ አራቱም የሰማይ ነፋሳት የሚመለከቱ አራት ቀንዶች ከበታቹ ወጡ። 9 ከእነርሱም ከአንደኛው አንድ ጠንካራ ቀንድ ወጣ፤ ወደ ደቡብም፥ ወደ ምሥራቅም፥ ወደ መልካሚቱም ምድር እጅግ ከፍ አለ። 10 እስከ ሰማይም ሠራዊት ድረስ ከፍ አለ፤ ከሰማይ ሠራዊትና ከሰማይ ከዋክብትም የተወሰኑትን ወደ ምድር ጣለ፥ ረገጣቸውም። 11 እስከ ሠራዊትም አለቃ ድረስ ምርኮን አዳነ፤ ከእርሱም የተነሣ የዘወትሩ መሥዋዕት ተሻረ፤ የመቅደሱም ስፍራ ፈረሰ። 12 የኀጢአትም መሥዋዕት ከዘወትሩ መሥዋዕት ጋር ተሰጠ፤ እውነትም ወደ ምድር ተጣለች፤ አደረገም፤ ተከናወነም። 13 ከቅዱሳኑም አንዱ ሲናገር ሰማሁ፤ ለተናገረው ለቅዱሱም ሁለተኛው ቅዱስ “ስለ ዘወትሩ መሥዋዕት፥ መቅደሱና ሠራዊቱም ይረገጡ ዘንድ ስለሚሰጥና ስለሚያጠፋ ኀጢአት የሆነው ይህ ራእይ እስከ መቼ ይቈያል?” አለው። 14 እርሱም፥ “እስከ ሁለት ሺህ ሦስት መቶ ማታና ጥዋት ድረስ ነው፤ ከዚያም በኋላ መቅደሱ ይነጻል” አለኝ። መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ራእዩን ለዳንኤል እንደ ተረጐመለት 15 እኔም ዳንኤል ራእዩን በአየሁ ጊዜ ልረዳው ፈለግሁ፤ እነሆም የሰው አምሳል በፊቴ ቆሞ ነበር። 16 በኡባልም ወንዝ መካከል የሰው ድምፅ ሰማሁ፤ ጠርቶም “ገብርኤል ሆይ! ራእዩን ለዚህ ሰው ግለጥለት” አለ። 17 እኔም ወደ ቆምሁበት ቀረበ፤ በመጣም ጊዜ ፈርቼ በግንባሬ ተደፋሁ፤ እርሱም፥ “የሰው ልጅ ሆይ! ራእዩ ለፍጻሜ ዘመን እንደ ሆነ አስተውል” አለኝ። 18 ሲናገረኝም ደንግጬ በምድር ላይ በግንባሬ ተደፋሁ፤ እርሱም ዳሰሰኝ፤ አንሥቶም በእግሬ አቆመኝ። 19 እንዲህም አለኝ- “እነሆ በመቅሠፍቱ በመጨረሻ ዘመን የሚሆነውን አስታውቅሃለሁ፤ ይህ ገና ለፍጻሜ ዘመን ነውና። 20 ያየኸው፥ ቀንዶች ያሉት አውራ በግ የሜዶንና የፋርስ ንጉሥ ነው። 21 አውራውም ፍየል የግሪኮች ንጉሥ ነው፤ በዐይኖቹም መካከል ያለው ታላቁ ቀንድ መጀመሪያው ንጉሥ ነው። 22 እርሱም በቆመበት በተሰበረ ጊዜ በእርሱ ፋንታ አራቱ እንደ ተነሡ፤ እንዲሁ ከወገኑ አራት መንግሥታት ይነሣሉ፤ ነገር ግን በኀይል አይተካከሉትም። 23 በመንግሥታቸውም መጨረሻ ኀጢአታቸው በተሞላች ጊዜ፥ እንቆቅልሽን የሚያስተውል፥ ፊቱ ጨካኝ የሆነ ንጉሥ ይነሣል። 24 ኀይሉም ይበረታል፤ በተአምርም ያጠፋል፤ ያደርግማል፤ ያከናወንማል፤ ኀያላንንና ቅዱሳንን ሕዝብ ያጠፋል። 25 ያንገቱን ቀንበር ያቀናል። ተንኰል በእጁ አለ፤ በልቡም ይታበያል፤ በሽንገላም ብዙዎችን ያጠፋል፤ በአለቆቹም አለቃ ላይ ይቆማል፤ ያለ እጅም ይሰብራል። 26 የተነገረውም የማታውና የጥዋቱ ራእይ እውነተኛ ነው፤ ነገር ግን ከብዙ ዘመን በኋላ ስለሚሆን ራእዩን ዝጋ።” 27 እኔም ዳንኤል ተኛሁ፤ አያሌም ቀን ታመምሁ፤ ከዚያም በኋላ ተነሥቼ የንጉሡን ሥራ እሠራ ነበር፤ ስለ ራእዩም አደንቅ ነበር፤ የሚያስተውለው ግን አልነበረም። |