ይህ መፅሐፍ በእግዚአብሔር አልተነፀረም እና የክርስቲያን ካኖን ወይም የአይሁድ ታናክ ክፍል አይደለም። ለታሪክና ለጥናት ዓላማ ብቻ ይታያል። ሙሉ ማብራሪያን ይመልከቱ ትንቢተ ዳንኤል 14 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)ምዕራፍ 14 ዳንኤልና የቤል ካህናት 1 ንጉሡ አስጢያጊስም ሞቶ በአባቶቹ መቃብር ከተቀበረ በኋላ የፋርሱ ንጉሥ ቂሮስ መንግሥቱን ያዘ። 2 ዳንኤልም የንጉሡ እልፍኝ አሽከር ነበረ፤ ከጓደኞቹም ሁሉ እርሱ ይከብር ነበር። 3 የባቢሎን ሰዎች የሚያመልኩት ስሙ ቤል የሚባል ጣዖት ነበር፤ ምግቡንም ሁልጊዜ ዐሥራ ሁለት ጫን በሚፈጅ ቻል ዐሥራ ሁለት መስፈሪያ ስንዴ፥ አርባ በግ፥ ስድስት ፊቀንም ወይን እያውጣጡ ይሰጡት ነበር። 4 ንጉሡም ያመልከው ነበር፤ ሁልጊዜም ወደ እርሱ እየሄደ ይሰግድለት ነበር፤ ዳንኤል ግን ለፈጣሪው ይሰግድ ነበር። ንጉሡም ዳንኤልን፥ “ለቤል የማትሰግድ ለምንድን ነው?” አለው። 5 ዳንኤልም ንጉሡን፥ “እኔስ ሰማይንና ምድርን የፈጠረ፥ ፍጥረትን ሁሉ የሚገዛ ሕያው አምላክን አመልካለሁ እንጂ የሰው እጅ የሠራው ጣዖትን አላመልክም” አለው። 6 ንጉሡም፥ “ቤል ሕያው ያልሆነ አምላክ ይመስልሃልን? በየቀኑ እንደሚበላና እንደሚጠጣ አታይምን?” አለው። 7 ዳንኤልም ሳቀና፥ “ንጉሥ ሆይ! አያስቱህ፤ ይህስ ውስጡ ጭቃ፥ ላዩም ናስ ነው፤ ፈጽሞም አይበላም፥ አይጠጣምም” አለው። 8 ንጉሡም ተቈጣ፤ የቤልን ካህናት ጠርቶ፥ “ይህን የቤልን ምግብ ማን እንደሚበላው ካልነገራችሁኝ ትሞታላችሁ። 9 ቤል እንደሚበላ ብታረጋግጡልኝ ግን ቤልን የፀረፈ ዳንኤል ይሞታል” አላቸው። ዳንኤልም ንጉሡን፥ “እንዳልኸው ይሁን” አለው። 10 ከሴቶቻቸውና ከልጆቻቸው በቀር የቤል ካህናት ሰባ ይሆኑ ነበር፤ ዳንኤልና ንጉሡም ወደ ቤል ቤት ሄዱ። 11 የቤል ካህናትም እንዲህ አሉ፥ “እነሆ እኛ ወደ ውጭ እንሄዳለን፤ ንጉሥ ሆይ! አንተም ማዕዱን ሥራ፤ ወይኑንም ቀድተህ አዘጋጅተህ አኑር፤ ደጃፉንም ዝጋ፤ በማኅተምህም አትመው። 12 ሲነጋም ሂድ፤ ቤል ሁሉን ሳይበላ ቢገኝ እኛ እንሞታለን፤ ካልሆነ ግን በእኛ ላይ ሐሰትን የተናገረ ዳንኤል ይሞታል” አሉት። 13 እነርሱ ግን የሚያደርጉትን ያውቁ ነበር፤ በማዕዱ በታች ስውር መግቢያ ነበራቸው፤ ሁልጊዜም በዚያ እየገቡ ይበሉ ነበር። 14 እነርሱም ከወጡ በኋላ ንጉሡ ለቤል የሚበላውን አዘጋጀ፤ ዳንኤልም ብላቴናውን አመድ ያመጣ ዘንድ አዘዘው፤ በንጉሡ ፊት ብቻ በቤቱ ሁሉ ነሰነሰው፤ ከወጡም በኋላ ደጃፉን ዘግተው በንጉሡ ማኅተም አተሙት። 15 እነርሱም ከሄዱ በኋላ የቤል ካህናት እንደ ልማዳቸው ከልጆቻቸውና ከሚስቶቻቸው ጋር በሌሊት ገብተው ሁሉንም በሉ፤ ጠጡም። 16 ንጉሡና ዳንኤልም በማለዳ ሄዱ። 17 ንጉሡም ዳንኤልን፥ “ማኅተሙ ደኅና ነውን?” አለው። ዳንኤልም፥ “ንጉሥ ሆይ፥ አወን ደኅና ነው” አለው። 18 ከዚህም በኋላ ደጃፉን በከፈተ ጊዜ ንጉሡ ማዕዱን እንደ ጨረሱት አገኘ፤ በታላቅ ድምፅም ጮኸ፥ “ቤል ሆይ! አንተ ታላቅ ነህ፤ መታለልም የለብህም” አለ። 19 ዳንኤልም ሳቀ፤ ንጉሡንም ያዘው፤ ወደ ውስጥም እንዳይገባ ከለከለው፤ “ወደ ምድር ተመልከት፤ ፍለጋውንም እይ፤ ይህ የምን ፍለጋ ነው?” አለው። 20 ንጉሡም፥ “የወንዶችንና የሴቶችን፥ የልጆችንም ፍለጋ አያለሁ” አለ። ንጉሡም ተቈጣ። 21 ያንጊዜም የቤልን ካህናት ሚስቶቻቸውንና ልጆቻቸውን ያዛቸው፤ በማዕዱም የተዘጋጀውን ይበሉና ይጠጡ ዘንድ የሚገቡበትን ስውር በር አሳዩት። 22 ስለዚህም ንጉሡ ገደላቸው፥ ቤልንም ለዳንኤል ሰጠው፤ ዳንኤልም ሰባበረው፤ ቤቱንም አፈረሰው። ዳንኤል ዘንዶውን እንደ ገደለ 23 በዚያም ስፍራ የባቢሎን ሰዎች የሚያመልኩት ታላቅ ዘንዶ ነበር። 24 ንጉሡም ዳንኤልን፥ “ይህንም ናስ ነው ትለዋለህን? እነሆ ሕያው ነው፤ ይበላል፤ ይጠጣልም፤ ሕያው አምላክ አይደለም ትለው ዘንድ አትችልም፤ ስለዚህ ስገድለት” አለው። 25 ዳንኤልም “ለፈጣሪዬ ለእግዚአብሔር እሰግዳለሁ፤ እርሱ ሕያው አምላክ ነውና። 26 ንጉሥ ሆይ! ይህን ዘንዶ ያለ ሰይፍና ያለ በትር እገድለው ዘንድ ፍቀድልኝ” አለው፤ ንጉሡም ዳንኤልን፥ “ፈቅጀልሃለሁ” አለው። 27 ዳንኤልም አደሮማርና ጠጕር ስብም አምጥቶ በአንድነት ቀቀለው፤ ልህሉህም አደረገው፤ ለዘንዶውም በአፉ አጐረሰው፤ ዘንዶውም በጐረሰው ጊዜ ተሰንጥቆ ሞተ፤ ዳንኤልም፥ “አምላካችሁን እዩ” አላቸው። 28 ከዚህ በኋላ የባቢሎን ሰዎች በሰሙ ጊዜ እጅግ ተቈጡ፤ በንጉሡም ላይ ተነሡ፤ እንዲህም አሉ፥ “ንጉሥ ይሁዳዊ ሆነ፤ ቤልን ሰበረ፤ ካህናቱንም አረደ፤ ዘንዶውንም ገደለ።” 29 ወደ ንጉሡም ሄዱ፤ እንዲህም አሉት፥ “ዳንኤልን ስጠን። ይህ ካልሆነ ግን ገንዘብህን እንዘርፋለን፤ እንገድልሃለን፤ ቤትህንም በእሳት እናቃጥላለን” አሉት። 30 ንጉሡም እጅግ እንዳስጨነቁት በአየ ጊዜ፥ ለንጉሡም ግዴታ በሆነበት ጊዜ ዳንኤልን አሳልፎ ሰጣቸው። 31 እነርሱም ወደ አንበሶች ጕድጓድ ጣሉት፤ በዚያም ስድስት ቀን ተቀመጠ። 32 በዚያም ሰባት አንበሶች ነበሩ። በየቀኑም ሁለት ሰውና ሁለት በግ ይመግቧቸው ነበር፤ ያንጊዜ ግን ዳንኤልን እንዲበሉት ምንም አልሰጧቸውም ነበር። 33 ነቢዩ ዕንባቆምም በይሁዳ ነበር፤ የምስር ንፍሮም አስቀቀለ፤ እንጀራም አስጋገረ፤ በቅርጫትም አድርጎ እህል ለሚያጭዱ ሰዎች ይዞ ወደ እርሻ ሄደ። 34 የእግዚአብሔርም መልአክ ዕንባቆምን፥ “ይህን ምሳ በባቢሎን በአንበሶች ጕድጓድ ላለው ለዳንኤል ውሰድ” አለው። 35 ዕንባቆምም፥ “አቤቱ! ባቢሎንን አላየሁም፤ የአንበሶችም ጕድጓድ ወዴት እንደ ሆነ አላውቅም” አለው። 36 የእግዚአብሔርም መልአክ በራሱ ጠጕር ተሸክሞ በመንፈስ ቅዱስ ኀይል በባቢሎን ወደ አለው ወደ አንበሶች ጕድጓድ አደረሰው። 37 ዕንባቆምም እንዲህ ብሎ ጮኸ፥ “ዳንኤል! ዳንኤል! እግዚአብሔር የላከልህን ይህን ምሳ ተቀበል” አለ። 38 ዳንኤልም፥ “ወዳጆቹን የማይዘነጋቸው እግዚአብሔር አሰበኝን?” አለ። 39 ዳንኤልም ተነሥቶ በላ፤ የእግዚአብሔርም መልአክ ዕንባቆምን ወዲያውኑ ወደ ሀገሩ መለሰው። 40 ንጉሡም በሰባተኛዪቱ ቀን መጥቶ ለዳንኤል አለቀሰለት፤ ወደ አንበሶቹም ጕድጓድ በቀረበ ጊዜ ዳንኤልን በአንበሶቹ መካከል ተቀምጦ አየው። 41 ንጉሡም በታላቅ ቃል ጮኸ፤ እንዲህም አለ፥ “የዳንኤል አምላክ እግዚአብሔር ሆይ! አንተ ታላቅ ነህ፤ ያለ አንተም ሌላ አምላክ የለም” አለ። 42 ዳንኤልንም ያንጊዜ ከአንበሶቹ ጕድጓድ አወጣው። ዳንኤልን ይገድሉት ዘንድ የወደዱ እነዚያንም ሰዎች ይዘው በአንበሶች ጕድጓድ ጣሏቸው፤ አንበሶቹም ወዲያውኑ በፊቱ በሉአቸው። ያንጊዜም ንጉሡ፥ “የሚያድን እርሱ ነውና በሰማይና በምድርም ምልክትንና ድንቅ ሥራን ያደርጋልና፥ ዳንኤልንም ከአንበሶች አፍ አድኖታልና ሁሉም የዳንኤልን አምላክ ያምልኩት” አለ። |