Biblia Todo Logo
የመስመር ላይ መጽሐፍ ቅዱስ
- ማስታወቂያዎች -

ይህ መፅሐፍ በእግዚአብሔር አልተነፀረም እና የክርስቲያን ካኖን ወይም የአይሁድ ታናክ ክፍል አይደለም። ለታሪክና ለጥናት ዓላማ ብቻ ይታያል። ሙሉ ማብራሪያን ይመልከቱ

መጽሐፈ ሲራክ 47 - መጽሐፍ ቅዱስ - (ካቶሊካዊ እትም - ኤማሁስ)


ናታን

1 ከእርሱም በኋላ በዳዊት ዘመን ትንቢት ለመናገር ናታን ተነሣ። ዳዊት

2 በኀብረት መሥዋዕት ላይ ስብ እንደሚለይ፥ ዳዊትም ከእስራኤላውያን መካከል እንዲሁ ተመረጠ።

3 ከግልገሎቹ እንደሚጫወት ከአንበሶች ጋር፥ ከጠቦቶች እንደሚጫወት ከድቦች ጋር ተጫወተ።

4 በልጅነቱስ ቢሆን ድንጋይ በመወንጭፍ ወርውሮ፥ ጉረኛው ጐልያድን ዘርሮ፥ ግዙፉን ሰው ጥሎ፥ የሕዝቡን እፍረት አልገፈፈምን?

5 ታላቁንና ኃያሉን ልዑል እግዚአብሔርን ለመነ፥ እርሱም ለቀኝ እጁ ብርታትን ሰጠው፥ የማይበገረውንም ጦረኛ በመግደል የወገኖቹን ብርታት ዳዊት አረጋገጠ።

6 ስለዚህም የዐሥር ሺህ ሰው ክብር ተሰጠው፥ ጌታን ባመሰገኑም ጊዜ፥ አሞገሱት የክብርም አክሊል ደፉለት።

7 በየግምባሩ ጠላቶቹን ደምስሷል፥ ፍልስጥኤማውያን ተቃዋሚዎቹን አጥፋቷል፤ ኃያልነታቸውንም ለምን ጊዜም አብስሯል።

8 በሥራዎቹ ሁሉ፥ ቅዱሱንና ኃያሉን እግዚአብሔርን ያመሰግናል። ለፈጣሪውም ባለው ጽኑ ፍቅር መንፈሱን ሁሉ በመዝሙሮቹ ላይ አሳረፈ።

9 በመሠዊያው ፊት መዘምራንን አቆመ፥ ጣዕመ ዜማቸውንም እንዲያሰሙ አደረገ።

10 ታላላቅ ግብሮችን አዘጋጀ፥ በዓላቱን በድምቀት አከበረ፥ የእግዚዘአብሔርን ቅዱስ ስም አመሰገነ፥ ቤተ መቅደሱም ከማለዳ አንስቶ በምስጋና ተሞላ።

11 ጌታ ኃጢአቱን ይቅር አለው፥ ከመቼውም በበለጠ ብርታትን ሰጠው፥ የንጉሥ ቃል ኪዳን ገባለት፥ በእስራኤልም ታላቅ ዙፋን ሰጠው።


ሰሎሞን

12 በእርሱ ምክንያት ሕይወቱን በተድላ ያሳለፈው ጥበበኛው ልጁ ዙፉኑን ወረሰ።

13 ሰሎሞን በነገሠበት ዘመን ሰላም ሰፈነ፥ በዙሪያውም ሁሉ እግዚአብሔር ሰላምን ሰጠው፥ ለስሙ መጠሪያ የሚሆን ቤት፥ ዘላለማዊ ቤተ መቅደሱንም ይሠራ ዘንድ አጨው።

14 ለጋ ወጣት ብትሆንም፥ እንደ ወንዝ በእውቀት የተሞላህ ጥበበኛ ነበርህ፥

15 መንፈስህ ምድርን ዳሰሳት፥ በምሥጢራዊ ዘይቤዎችህም ሞላሃት፥

16 ዝናህ እሩቅ በተባሉት ደሴቶች ላይ እንኳ ናኝቷል፥ ስለ ሰላምህም የተወደድህ ነበርህ።

17 መዝሙሮችህ፥ ምሳሌዎችህ፥ ዘይቤዎችህ፥ መልሶችህም በዓለም ዙሪያ አድናቆትን አትርፈዋል።

18 በጌታ በእግዚአብሔር፥ የእስራኤል አምላክ በሆነው በእርሱ ስም፥ ወርቅ እንደ ቆርቆሮ ብርም እንደ እርሳስ ሰበሰብህ።

19 ሥጋህን ለሴቶች ሰጠህ፥ የፍላጐትህም ተገዥ ሆነህ፥

20 ክብርህን አሳደፍህ፥ ዘርህን አረከስና፥ በልጆችህ ላይ ቅጣትን አመጣህ፥ በዕብደትህም መከራ ወረደባቸው።

21 መንግሥትህ ከሁለት ተከፈለ፥ ከኤፍሬምም ዓመፀኛ መንግሥት ተነሣ።

22 ጌታ ግን መሐሪ ነው፥ ቃሉን አያጥፍም፥ ለመረጠው ዘር አይነሣም፥ የወደደውንም ሰው ዘር አያጠፋም። እነሆ ለያዕቆብ ምትክ ተወለት፥ ለዳዊትም ከእርሱ የሚወጣ ሥር ሰጠው።


ሮብዓም

23 ሰሎሞን ከአባቶቹ ጐን አረፈ፥ ዙፋኑን ለልጆቹ አንዱ፥ ከሕዝቡ መካከል እጅግ የማይረባው፥ ማስተዋል የጐደለውና ሕዝቡንም ለዓመፅ የገፋፋው ሮብዓም ወረሰ።

24 የናባጥ ልጅ ኢዮርብዓም እስራኤልን አሳሳተ፥ ኤፍሬምንም በክፋት መንገድ መራው፤ ከዚያም ወዲህ ኃጢአታቸው እጅግ በረከተ፤ ከሀገራቸውም እስኪወጡ አደረሳቸው፤

25 ፍዳው እስከመጣባቸውም ጊዜ ድረስ፥ ያልፈጸሙት ኃጢአት አልነበረምና።

ተከተሉን:



ማስታወቂያዎች