ይህ መፅሐፍ በእግዚአብሔር አልተነፀረም እና የክርስቲያን ካኖን ወይም የአይሁድ ታናክ ክፍል አይደለም። ለታሪክና ለጥናት ዓላማ ብቻ ይታያል። ሙሉ ማብራሪያን ይመልከቱ መጽሐፈ ሲራክ 15 - መጽሐፍ ቅዱስ - (ካቶሊካዊ እትም - ኤማሁስ)1 እግዚአብሔርን የሚፈራ ሰው ይህን ሁሉ ያደርጋል፤ ሕግን አጥብቆ የሚይዝ ጥበብን ያገኛል። 2 ጥበብ እንደ እናት ሆና ልታገኘው ትመጣለች፤ እንደ ድንግል ሙሽራ ሆና ትቀበለዋለች። 3 የዕውቀት እንጀራ ታቀርብለታለች፤ የጥበብን ውሃ ታጠጣዋለች። 4 እርሱም እርሷን ይደግፋል፥ አይወድቅምም፥ በእርሷ ይተማመናል፥ አያፍርም። 5 ከባልንጀሮቹ በላይ ከፍ ታደርገዋለች፥ በስብሰባ መካከል እንዲናገር አፉን ትከፍትለታለች። 6 ደስታና የደስታ አክሊል ይቀበላል፤ ዘላለማዊ ስምም ይወርሳል። 7 አላዋቂዎች ግን አያገኟትም፥ ኃጢአተኞች አያዩዋትም። 8 ከትዕቢተኛ ትርቃለች፤ ሐሰተኞች አያስታውሷትም። 9 ከኃጢአተኛ አፍ ምስጋና አይጠበቅም፤ ጌታ በዚያ አላኖረውምና። 10 ምስጋና በጥበብ ይነገራል፤ የሚያነሳሳውም እግዚአብሔር ነው። የምርጫ ነጻነት 11 የሚጠላውን አይፈጥርምና ኃጢአት እንድሠራ ምክንያት የሆነኝ ጌታ ነው አትበል። 12 እግዚአብሔር ሐሳቡን ለመፈጸም ኃጢአተኛ እንዲረዳው አያስፈልገውምና፥ ኃጢአት እንድሠራ ያደረገኝ እሱ ነው አትበል። 13 ጌታ ክፉ ነገርን ሁሉ ይጠላል፤ እርሱን የሚፈራም ክፋትን አይወድም። 14 በመጀመሪያ ሰውን የፈጠረ እሱ ነው፤ ሰው በገዛ ሐሳቡ እንዲመራ ተወው። 15 ከፈለግህ ትእዛዛቱን ታከብራለህ፤ ለእርሱም ፈቃድ ትታመናለህ። 16 ከፊትህ እሳትና ውሃ አስቀምጧል፤ በምትሻው ውስጥ እጅህን ጨምረው። 17 ለሰዎች ሕይወትና ሞት ቀርበውላቸዋል። ለእያንዳንዱም ሰው የመረጠው ይሰጠዋል። 18 የጌታ ጥበብ ሰፊ ነውና፥ እርሱ ኃያልና ሁሉን የሚያይ ነው። 19 ዐይኖቹም የሚመለከቱት ወደሚፈሩት ሰዎች ነው፤ እሱ የሰዎችን ሥራ ሁሉ ያውቃል። 20 ሰው ክፉ እንዲሆን አላዘዘም፥ ሰው ኃጢአት እንዲሠራ አልፈቀደም። |