ይህ መፅሐፍ በእግዚአብሔር አልተነፀረም እና የክርስቲያን ካኖን ወይም የአይሁድ ታናክ ክፍል አይደለም። ለታሪክና ለጥናት ዓላማ ብቻ ይታያል። ሙሉ ማብራሪያን ይመልከቱ መጽሐፈ ዮዲት 3 - መጽሐፍ ቅዱስ - (ካቶሊካዊ እትም - ኤማሁስ)1 ስለዚህ ሰላምን የሚለምኑ መልዕክተኞችን እንዲህ በማለት ላኩበት፦ 2 “እነሆ፥ እኛ የታላቁ ንጉሥ የናቡከደነፆር አገልጋዮች በፊትህ እጅ እንነሣለን፥ በፊትህ እንደ ወደድህ አድርገን። 3 እነሆ መኖሪያዎቻችን፥ መሬታችን ሁሉ፥ እርሻዎቻችን፥ መንጋዎቻችን፥ በጐቻችንና የመሰማሪያችን ቦታዎች ሁሉ፥ በፊትህ ናቸው፤ እንደ ወደድህ አድርጋቸው። 4 እነሆ ከተሞቻችንና የሚኖሩባቸውም ሁሉ ባርያዎችህ ናቸው። መጥተህም ለዓይንህ መልካም የሆነውን አድርግ።” 5 ሰዎቹ ወደ ሆሎፎርኒስ መጥተው ይህንኑ ነገሩት። 6 እርሱም ከሠራዊቱ ጋር ወደ ባሕሩ ጠረፍ ወርደ፥ በተመሸጉት ከተሞችም የጦር ሰፈር አቆመ፤ እንዲረዱትም ከእነርሱ የተመረጡ ሰዎችን ወሰደ። 7 እነሱና በዙሪያውም ያሉ አገሮች ሁሉ አክሊል ደፍተው በጭፈራና በከበሮ ተቀበሉት። 8 እርሱ ግን አገራቸውን ሁሉ አጠፋ፥ የማምለኪያ ዐፀዶቻቸውንም ቆረጠ፤ ሕዝቦች ሁሉ ናቡከደነፆርን ብቻ እንዲያመልኩና ቋንቋዎችና ነገዶች ሁሉ አምላክ ብለው እንዲጠሩት፥ የምድሪቱን አማልክት እንዲያጠፋ ታዝዞ ነበርና። 9 ከይሁዳ ተራሮች አንፃር በዶታን አጠገብ ወደሚገኝ ወደ ኤስድራሎን መጣ። 10 በጌባና በሲቶፖሊስ መካከል ሰፈረ፥ ለሠራዊቱ ስንቅ ለመሰብሰብ በዚያ አንድ ወር ሙሉ ተቀመጠ። |